መንበራቸውን ከቀድሞው ቤልጀማዊው አሰልጣኝ ፖል ፒዩት የተረከቡት ከአራት ወራት በፊት ነው፡፡ ይሁን እንጂ የሃገሪቱ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከተቀጠሩ ጀምሮ የከፈላቸው የሁለት ወራት ደሞዝ ብቻ ነው፡፡ አሁንም ቢሆን የሐምሌና የነሃሴ ወር ደሞዝ እስካሁን አልተከፈላቸውም፡፡
ሴባስቲያን ሚኜ በባለፉት ሁለት ዓመታት ብቻ የሐራምቤ ከዋክብቱን የመሩ አምስተኛ የውጭ ሃገር አሰልጣኝ ናቸው፡፡ ሚስተር ሚኜ በፌዴሬሽኑ አሰራር መንገፍገፋቸውን የተረዳው የኬንያ እግር ኳስ ብሔራዊ ቡድን ምትካቸውን ካሁኑ ማፈላለግ ጀምሯል፡፡ ከለቀቁም መንበራቸውን የአሁኑ የጎር ማህያ አሰልጣኝ ዳይላን ኬር ሊረከቡት ይችላሉ፡፡ ለዚህም ነው የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት ለጎር ማያ ክለብ የሰውዬውን የትምህርትና የሥራ ማስረጃ እንዲልኩለት ደብዳቤ መጻፉ፡፡ የኬንያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለአሰልጣኙ ስምንት ሚሊዮን የኬንያ ሽልንግ ባለዕዳ ነው፡፡
የብሔራዊ ቡድኑ ዕዳ ይህ ብቻ አይደለም፤ የማላዊን የወዳጅነት እና የጋናን የማጣሪያ ጨዋታ ካሸነፋችሁ ተብሎ የተገባላቸው እጅ መንሻ እስካሁን ያልተከፈላቸው የሐራምቤ ከዋክብት ቃል የተገባልንን አስራ ዘጠኝ ሚሊዮን ሽልንግ ወዴት ዘወር አደረጋችሁብን ብለው ፌዴሬሽኑ ላይ መጉረጥረጣቸውን ቀጥለዋል፡፡
በፌዴሬሽኑ ሥነ-ምግባር እጅግ የተበሳጩት ፈረንሳያዊ ከበር ቆመዋል፤ ሁለት ሶስት ጊዜም መልቀቂያቸውን ለማስገባት ሞክረው እንደነበር ነው የተገለጸው፡፡ አሰልጣኙ ደሞዛቸው በቅርቡ ካልተሰጣቸውም ከዚህ በፊት የሃገሪቱን ብሔራዊ ቡድን እንዳሰለጠኑት ስኮትላንዳዊው ቦቢ ዊሊያምሰን እና ቤልጀማዊው አዴል አምሩሽ እሳቸውም ፌዴሬሽኑን ችሎት ፊት ገትረው ለመቀበል ያስባሉ፡፡
መስከረም 30 ባህር ዳር ላይ እንዲሁም ከሶስት ቀናት በኋላ ጥቅምት 3 ቀን ናይሮቢ ላይ ኢትዮጵያን የሚገጥመው ቡድን ለደርሶ መልሱ ጨዋታ ማትጊያ 26 ሚሊዮን ሽልንግ ቃል ቢገባለትም ተጫዋቾቹ ግን ጽድቁ ቀርቶ በቅጡ በተኮነንን እያሉ ነው፡፡ ለማንኛውም ጋናን 1-0 በረታው የኬንያ ብሔራዊ ቡድን ውስጥ የሚሰማው ነገር ፌሽታ ብቻ አይመስልም፡፡
አስተያየት ይስጡ