በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 5ኛ ሳምንት 8ጨዋታዎች በሳምንቱ መጨረሻ እና በቀጣዩ ሳምንት መጀመሪያ የሚካሄዱ ሲሆን ሁሉም ጨዋታዎች በክልል የሚደረጉ ይሆናል። ከሚደረጉት ጨዋታዎች መካከል 6ቱ ጨዋታዎች ቅዳሜ ሲደረጉ እሁድ እና ሰኞ ደግሞ አንድ አንድ ጨዋታ የሚደረጉ ይሆናል። ከነዚህ ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን በዚህ ቅድመ ዳሰሳ ለእናንተ እንዲስማማ አድርገን አቅርበንላችኋል።
ጨዋታ 1
ድሬዳዋ ከተማ ከኢትዮጲያ ቡና
የጨዋታ ቀን: ቅዳሜ ታህሳስ 18/2012
የጨዋታ ሰዓት: 9:00
የጨዋታ አርቢትር: ፌደራል አርቢትር አዳነ ወርቁ
አራተኛውን ሳምንት በተለያየ ውጤት ያሳለፉት ሁለቱ ቡድኖች ጨዋታቸውን የሚያደርጉ ይሆናል። በአሰልጣኝ ስምዖን አባይ የሚሰለጥኑት ድሬዳዋ ከተማዎች በዘንድሮው የውድድር ዓመት አስከፊ የተከላካይ ክፍል ያለው ቡድን ሲሆን እስካሁን በሊጉ 11 ግቦች ሲቆጠሩበት በሁለት ጨዋታዎች ብቻ 9ግቦች ተቆጥረውበት በሊጉ ከፍተኛ ግብ የተቆጠረበት ቡድን ሆኗል። ኢትዮጵያ ቡና በአንፃሩ በአሰልጣኝ ካሳዬ አራጌ እየተመራ ከጨዋታ ጨዋታ መሻሻልን እያሳየ እንዳለ ለማስተዋል ተችሏል። በ4ኛው ሳምንት ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ ወደ ባህርዳር ተጉዞ በባህርዳር ከተማ የ4-1 አስደንጋጭ ሽንፈት ሲያስተናግድ ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ አ.አ ስቴዲየም ላይ በሊጉ ጥሩ አጀማመር ማድረግ ችሎ የነበረውን ሀዋሳ ከተማን አስተናግዶ በእንዳለ ደባልቄ ሀትሪክ ታግዞ 4-1 ማሸነፉ ይታወሳል። በሊጉ ሰንጠረዥ ድሬዳዋ ከተማ በ3ነጥቦች እና በ8የግብ እዳ 15ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ኢትዮጵያ ቡና በ5ነጥቦች 9ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
በድሬዳዋ ከተማ በኩል ያሬድ ሃሰን እና ግብ ጠባቂው ሳምሶን አሰፋ ከጉዳት ሲያገግሙ ምንያህል ተሾመ እና ረመዳን ናስር በጉዳት ከነገው ጨዋታ ውጪ ናቸው። በኢትዮጵያ ቡና በኩል ታፈሰ ሰለሞን እና አቡበከር ናስር በጉዳት ምክንያት የማይጫወቱ ይሆናል።
ጨዋታ 2
ሀዲያ ሆሳዕና ከባህርዳር ከተማ
የጨዋታ ቀን: ቅዳሜ ታህሳስ 18/2012
የጨዋታ ሰዓት: 9:00
የጨዋታ አርቢትር: ኢንተርናሽናል አርቢትር ብሩክ የማነብርሃን
በሌላ የሊጉ የ9 ሰዓት ጨዋታ ሆሳዕና ላይ ሀዲያ ሆሳዕና ከባህርዳር ከተማ የሚያደርጉት ጨዋታ ይሆናል። ኢንተርናሽናል አርቢትር ብሩክ የማነብርሃን የሚመራው ይህ ጨዋታ ለሁለቱም ቡድኖች በጣም ወሳኝ ነው። ሀድያ ሆሳዕና በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ ባህርዳር ከተማ ደግሞ ድል በማስመዝገብ ከመሪው ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ለማጥበብ የሚያደርገው ጨዋታ በመሆኑ በጉጉት እንዲጠበቅ ያደርገዋል። ሀድያ ሆሳዕና በ4ኛው ሳምንት ወደ ወደ ጎንደር ተጉዞ በፋሲል ከተማ የ3-0 ከባድ ሽንፈት ሲያስተናግድ ባህርዳር ከተማ በአንፃሩ በሜዳው ድሬዳዋ ከተማን ገጥሞ 4-1 በማሸነፍ ጣፋጭ ድል ማስመዝገቡ ይታወሳል። ሁለቱ ቡድኖች ባደረጓቸው 4የሊጉ ጨዋታዎች ሀድያ ሆሳዕና በ1ነጥብ እና በ5 የግብ ዕዳ የሊጉ ግርጌ ላይ ሲገኝ ሲገኝ ባህርዳር ከተማ ደግሞ በ7ነጥቦች 3ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
በሀድያ ሆሳዕና በኩል አብዱልሰመድ ዓሊ በጉዳት እንዲሁም ሱራፌል ዳንኤል ደግሞ በ4ኛው ሳምንት ከፋሲል ከተማ ጋር ሲጫወት በተመለከተው ቀይ ካርድ ምክንያት በነገው ጨዋታ የማይሰለፍ ይሆናል። ይህን ዳሰሳ እስካጠናከርንበት ጊዜ ድረስ በባህርዳር ከተማ በኩል የተሰማ ጉዳትም ሆነ ቅጣት የለም።
አስተያየት ይስጡ