ከሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታዎች መካከል ዛሬ አዲስአበባ ላይ የሚካሄደውን የሰበታና ፋሲል ጨዋን በዳሰሳችን እንደሚከተለው ተመልክተነዋል ።
የኢትዮጵያ ኘሪምየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት ስድስት ጨዋታዎች ትናንት ሲደረጉ ዛሬ እሁድ በብቸኝነት በአዲስአበባ ስታዲየም የሰበታና ፋሲል ጨዋታ ይጠበቃል ።
የዛሬ ውጤቶችን ተከትሎ ወደ ወራጂ ቀጠና የገባው ሰበታ ከተማ በነገው ጨዋታ ውጤት አስመዝግቦ ከጫና ለመውጣት እንደሚፋለም ሲጠበቅ አፄዎቹ በበኩላቸው ሰበታን አሸንፈው የሊጉን መሪነት ለመቆናጠጥ ከዚህ ጨዋታ ሙሉ ነጥብ እንደሚያስፈልጋቸው ሲታሰብ ጨዋታው የበለጠ ከወዲሁ አጓጊ ሁኗል ።
ባለፈው የውድድር ዓመት ከፋሲል ከነማ ጋር ስኬታማ ጊዜን ያሳለፉት አሰልጣኝ ውበቱ አባተ አሁን ደግሞ የሊጉ አዲስ አዳጊውን ሰበታ ከተማ ይዘው የቀድሞ ክለባቸውን ፋሲል የሚገጥሙበት ጨዋታ ትልቅ ትኩረት ካገኙ የሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታዎች መካከል ቀዳሚው ነው ።
በሁለት ጨዋታዎች ከሜዳው ውጪ የአንድ ጨዋታ ሽንፈትና የአቻ ውጤት ያስመዘገበው ፋሲል ከነማ በዚህኛው ሳምንት ከባለሜዳው ሰበታ ከተማ ጋር መገናኘቱና የሰበታ ስታድየም እድሳት ባለመጠናቀቁ ጨዋታው አዲስአበባ ላይ የሚካሄድ መሆኑ ፋሲል የተሻለ ተጠቃሚ እንደሚሆን የሚታሰብ ቢሆንም በውጤት ማጣት ውስጥ ከሚገኘውና እያንሰራራ ካለው ሰበታ ከተማ ላይ ድል ለመቀዳጀት ብርቱ ጥንካሬን ይጠይቃል ።
ሰበታ ከተማ ባለፉት አራት ሳምንታት ጨዋታዎች በሁለት ጨዋታ ሽንፈት አስተናግደው በአንድ ጨዋታ አቻ ሲለያዩ ባለፈው ሳምንት ደግሞ ወልቂጤ ከተማን አሸንፈው
በደረጃ ሰንጠረዡ በአራት ነጥብ አስራ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠው አፄዎቹን በሜዳቸው ያስተናግዳሉ።
የሜዳቸውን ያህል ከሜዳቸው ሲወጡ ምቾት ተሰምቷቸው በበርካታ ደጋፊዎቻቸው ፊት በሚጫዎቱበት በአዲስአበባ ስታዲየም ጠንካራውን ሰበታ የሚገጥሙት አፄዎቹ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ከሜዳቸው ወጥተው ሙሉ ሶስት ነጥብ ባያገኙም የቡድኑ ጎል የማስቆጠር ችግር በትንሹም ቢሆን ተስፋ የሚጣልበት እንደመሆኑ ከጨዋታው ሙሉ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ወደ ሜዳ እንደሚገቡ ይጠበቃል ።
የጨዋታውን የበላይነት ለመውሰድ መሃል ሜዳ ላይ የፋሲሉ አማካይ የሱራፌል ዳኛቸውና የሰበታው ዳዊት እስጢፋኖስ የሚያደርጉት ፍልሚያ ይጠበቃል ። የሁለቱም ቡድኖች አሰልጣኞች ቅድሚ የኳስ ቁጥጥር የበላይነትን ወስደው መጫዎትን የሚመርጡ እንደመሆናቸው በዛሬው ጨዋታ በሁለቱ አሰልጣኞች በኩል የታክቲክ ለውጥ እንደሚኖር የሚጠበቅ ነው ።
በዛሬ ጨዋታ አንተነህ ተስፋዬ እና ባኑ ዱያዋራ ሰበታ ከተማን በጉዳት ምክንያት አገልግሎት አይሰጡም ።
የአፄዎቹን ቤት የጉዳት ዜና ስንመለከት አብዱራህማን ሙባረክ ፣መልካሙ ታውፈር ፣እንየው ካሳሁን፣አቤል እያዩ ፣ኤፍሬም ክፍሌና ሰለሞን ሀብቴ ለዚህ ጨዋታ እንደማይደረሱ የተረጋገጠ ሲሆን አምበሉ ያሬድ ባየ ግን ከጉዳቱ እንዳገገመና ለዛሬው ጨዋታ በጥሩ የአካል ብቃት ላይ እንደሚገኝ ተረጋግጧል ።
አስተያየት ይስጡ