የኢትየጵያ ፕሪምየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት ተስተካካይ ጨዋታ ቅድመ ዳሰሳ
በኢትየጵያ ፕሪምየር ሊግ 14ኛ ሳምንት ተስተካካይ አንድ ጨዋታ ዛሬ የሚደረግ ይሆናል።
ጅማ ላይ በሚደረገው የዕለተ ማክሰኞ ብቸኛ የሊጉ ተስተካካይ ጨዋታ 9፡00 ሲል ጅማ አባጅፋርን ከ ወላይታ ድቻ የሚያገናኝ ይሆናል።
በ14ኛው ሳምንት በዕለተ እሁድ ጥር 27/2010 ዓ.ም ሊካሄድ ቀጠሮ ተይዞለት የነበረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ወላይታ ድቻ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ዋንጫ በነበረበት የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ዝግጅት ምክንያት በተያዘለት ቀን ሳይደረግ ቀርቶ ለዛሬ መተላለፉ የሚታወቅ ነው።
በአሰልጣኝ ገ/መድህን ኃይሌ የሚመራው ጅማ አባጅፋር በዘንድሮው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ጥሩ ብቃት እያሳዩ ከሚገኙ ቡድኖች ውስጥ የሚጠቀስ ሲሆን በሊጉም 5ኛ ደረጃ መቀመጥ ችሏል። ጅማ አባጅፋር በ15ኛው ሳምንት ከአዳማ ከተማ ጋር አቻ ከተለያየ በኋላ ያለፉትን 15 ቀናት እረፍት ላይ እንደነበር ይታወቃል።
ወላይታ ድቻ በአንፃሩ በሊጉ ጅማሬ ላይ ወጥ አቋም ማሳየት ተስኖት በሊጉ ግርጌ ላይ ለመቀመጥ ተገዶ ነበር። ሆኖም የአሰልጣኝ መሳይ ተፈሪን ስንብት ተከትሎ አሰልጣኝ ዘነበ ፍስሀ ቡድኑን ከተረከቡት በኋላ እጅግ ከፍተኛ መሻሻሎችን አሳይቶ ከወራጅ ቀጠናው በመውጣት 9ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።
በ15ኛው ሳምንት ጨዋታ ጅማ አባጅፋር ወደ አዳማ ተጉዞ ከአዳማ ከተማ ጋር ያደረገውን ጨዋታ ከመመራት ተነስቶ 1-1 በሆነ አቻ ውጤት አጠናቆ ሲመለስ ወላይታ ድቻ ከወልዲያ ስፖርት ክለብ ሊያደርገው የነበረው ጨዋታ ወላይታ ድቻ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ዋንጫ በነበረበት የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ዝግጅት ምክንያት ለመጋቢት 1/2010 ዓ.ም ተዛውሯል።
በአጠቃላይ በዘንድሮው በሊጉ ጅማ አባጅፋር ካደረጋቸው 14ጨዋታዎች በ6ቱ አሸንፎ በ4ቱ አቻ ተለያይቶ በ4 ተሸንፎ ማግኘት ከሚገባው 42 ነጥቦች 22ቱን አሳክቶ በሊጉ 5ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ሲችል 2ተስተካካይ ጨዋታዎች የሚቀሩት ወላይታ ድቻ በአንፃሩ 13 ጨዋታዎችን አከናውኖ 4ጨዋታዎችን አሸንፎ በ4ቱ አቻ ወጥቶ በ5ቱ ተሸንፎ ከተጋጣሚው ጅማ አባጅፋር በ6ነጥቦች በማነስ በ16 ነጥቦች 9ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።
ኢንተርናሽናል አርቢትር ዳዊት አሳምነው የሚመሩት የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ልክ 09:00 ሲል በጅማ ስታዲየም የሚካሄድ ይሆናል።
አስተያየት ይስጡ