የቶታል የአፍሪካ ኮንፈደሬሽን ዋንጫ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ቅደመ ዳሰሳ
በ2018 የቶታል የአፍሪካ ኮንፈደሬሽን ዋንጫ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ የኢትዮጵያው ወላይታ ድቻን ከዛንዚባሩ ዚማሞቶ ጋር የሚያገናኘው ጨዋታ ዛሬ ሀዋሳ ኢንተርናሽናል ስታዲየም ላይ የሚደረግ ይሆናል። ከ10 ቀናት በፊት ዛንዚባር ላይ ያደረጉትን ጨዋታ 1-1 በሆነ አቻ ውጤት ማጠናቀቃቸው የሚታወስ ነው። በጨዋታው ወሳኟን ከሜዳ ውጪ የተገኘች ግብ ማስቆጠር የቻለው አጥቂው ጃኮ አረፋት እንደነበር አይዘነጋም።
ሁለቱ ቡድኖች ወደዚህ ውድድር እንዴት በቁ?
ወላይታ ድቻ ለዚህ ውድድር የበቃው የ2009 ዓ.ም የኢትዮጵያ ጥሎ ማለፍ ዋንጫን በማሸነፍ ሲሆን ዚማሞቶም የዛንዚባርን ዋንጫ በማሸነፍ ለዚህ ውድድር መቅረብ ችሏል።

የሁለቱ ቡድኖች የአፍሪካ መድረክ ታሪክ
ወላይታ ድቻ፦ በአፍሪካ መድረክ ሲሳተፍ የመጀመሪያው ነው።
ዚማሞቶ፦ የዘንድሮው ውደድር በአፍሪካ ኮንፈደሬሽን ካፕ የመጀመሪያ ተሳትፎው ሲሆን በአፍሪካ ቻምፒዮንስ ሊግ ግን 1 ጊዜ (2017) ተሳትፎ በቅድመ ማጣሪያው ከውድድሩ ሊሰናበት ችሏል።

የሁለቱ ቡድኖች አሰልጣኞች ስለጨዋታው ምን አሉ?
አሰልጣኝ ዘነበ ፍስሀ — ወላይታ ድቻ
“ያለው ነገር እጅግ በጣም ጥሩ ነው፤ በዚማሞቶ በኩል አብዛኛውን ጊዜ ከመስመር በሚነሱ ኳሶች ስለሚጫወቱ እሱን ለመመከት ስራዎችን ሰርተን ተዘጋጅተናል። ዚማሞቶ ጥሩ ቡድን ነው፤ እኛ ነጥብ በመጋራታችን እነሱን አቅልለን የምንገባ አይሆንም፤ እንደ ማንኛውም ጨዋታ ነው፤ የጨዋታ ትንሽ እና ትልቅ የለውም።” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
አሰልጣኝ ሞሱማ አብዱላሂ —- ዚማሞቶ
“እዚህ የመጣነው የሚቻለንን ሁሉ ለማድረግ ነው፤ ምክንያቱም ወላይታ ድቻ ከኛ የተሻለ እድል አላቸው፤ ከሜዳቸው ውጪ ጎል ማስቆጠራቸው በትልቅነቱ ይጠቅማቸዋል። ስለዚህ አማራጭ ስለሌለን ከባድ ፍልሚያ አድርገን ግብ ለማስቆጠር ወደ ሜዳ እንገባለን።” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ቡድናቸውን ለመደገፍ በርከት ያሉ ደጋፊዎች ከሶዶ ተነስተው 104ኪ.ሜ አቋርጠው ሀዋሳ የገቡ ሲሆን ነገ ደግሞ በርከት ያሉ ደጋፊዎች ከይርጋለም ተነስተው ወደ ሀዋሳ ለመጓዝ ዝግጅታቸውን እንዳጠናቀቁ የደረሰን መረጃ ያመላክታል።


የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ዛሬ 10:00 ሲል በሀዋሳ ኢንተርናሽናል ስታዲየም የሚደረግ ይሆናል።
አስተያየት ይስጡ