በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ ግብር ትላንት አዲስ አበባ ስታዲየም ላይ እንዲካሄድ ፕሮግራም ተይዞለት የነበረው የቅዱስ ጊዮርጊስና የሀዋሳ ከተማ ጨዋታ 0-0 በሆነ አቻ ውጤት ተጠናቋል።
ይህ ጨዋታ በትናንትናው እለት ሊደረግ ቀጠሮ ተይዞለት የነበረ ቢሆንም ጨዋታው ከመጀመሩ በፊት በደጋፊዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት ጨዋታው ሳይካሄድ መቅረቱ ይታወሳል፡፡

በዛሬው እለትም ሀዋሳ ከተማዎች ጨዋታውን አናካሂድም በማለት ወደ ሀዋሳ ጉዞ ከጀመሩ በኋላ ከዝዋይ ከተማ ዳግም ወደ አዲስ አበባ ተመልሰው ጨዋታውን አድርገዋል፡፡ ጨዋታውም በዝግ ስታዲየም የተካሄደ ሲሆን ያለግብ በአቻ ውጤት ሊጠናቀቅ ችሏል፡፡
በጨዋታው በሁለቱም ቡድኖች በኩል የረባ እንቅስቃሴ ያልተደረገበት ሲሆን ሁለቱም ቡድኖች ቀጥተኛ አጨዋወትን ምርጫቸው አድርገው ሲጫወቱ ተስተውለዋል። ፈረሰኞቹ በረጃጅም ኳሶች ወደ ተጋጣሚያቸው የግብ ክልል ለመድረስ ጥረት ሲያደርጉ ሀዋሳ ከተማዎች በበኩላቸው በመልሶ ማጥቃት ወደ ግብ ለመድረስ ጥረት ቢያደርጉም አንድም የረባ ሙከራ ማድረግ ሳይችሉ ተጉዘዋል። በመጀመሪያው አጋማሽ የቅ/ጊዮርጊሱ አቤል ያለው ከሞከራቸው ኳሶች በስተቀር ይህ ነው የሚባል የጨዋታ እንቅስቃሴ ሳይስተዋልበት የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ ችሏል።
ሁለተኛው አጋማሽም እንደ መጀመሪያው አጋማሽ ሁሉ የረባ እንቅስቃሴ ያልታየበት ነበር፡፡ በዚህ አጋማሽም ከ1አመት በላይ በጉዳት ከሜዳ ርቆ የነበረው ሰልሀዲን ሰዒድ በኃይሉ አሰፋን ተክቶ በመግባት የመጀመሪያ ጨዋታውን ማድረግ ችሎ ነበር፡፡
62ኛው ደቂቃ ላይ የሀዋሳ ከተማው እስራኤል እሸቱ በግል ጥረቱ ያገኘውን ኳስ ወደ ግብ ሞክሮት የቅ/ጊዮርጊሱ ግብ ጠባቂ ማታሲ አድኖበታል። 65ኛው ደቂቃ ላይ የቅ/ጊዮርጊሱ አጥቂ አቤል ያለው ከመስመር የተሻገረለትን ኳስ ሞክሮ ወደ ውጭ ወጥቶበታል። ከዚህች ሙከራ 5ደቂቃዎች በኋላ 70ኛው ደቂቃ ላይ የቅ/ጊዮርጊሱ አማካይ ናትናኤል ዘለቀ ከሀዋሳዎች ሳጥን ውጭ በቀጥታ የሞከረው ኳስ በግቡ አግዳሚ ላይ ለጥቂት ወደ ውጭ ወጥቷል።
በዚህም ጨዋታው ምንም ግብ ሳይስተናገድበት 0-0 በሆነ ውጤት ሊጠናቀቅ ችሏል። ውጤቱንም ተከትሎ ሀዋሳ ከተማ 11 ነጥቦችን በመሰብሰብ መሪነቱን ሲያስቀጥል ቅ/ጊዮርጊስ በአንፃሩ በ4ነጥቦች 10ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።
አስተያየት ይስጡ