ጨዋታዉ በሁለቱም ቡድን በኩል ተመጣጣኝ በሆነ በፈጣን እንቅስቃሴ የጀመረ ሲሆን ገና ከጅምሩ ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን ሲሞክሩ ነበር።
ለአብነትም በወልቂጤ በኩል ጌታነህ ከበደ በቅጣት ምት የመታት ኳስ በግብ ጠባቂዉ ዳንኤል ተሾመ የተመለሰበት አጋጣሚ እና በድሬዎች በኩል በቢንያም ጌታቸዉ የተገኘ ለጎል የሚሆን ኳስ በግብ ጠባቂዉ ጀማል ጣሰዉ የተመለሰበት ተጠቃሽ ነዉ።
ጨዋታዉ ከእዛ በኋላ በሁለቱም ቡድኖች በኩል ቀዝቃዛ እንቅስቃሴ ሲስተዋልበት የነበረ ሲሆን በአንፃራዊነት የድሬዎች እንቅስቃሴ የተሻለ ነበር።
- ማሰታውቂያ -
በ38ኛዉ ደቂቃ እያሱ ለገሰ ለድሬዳዋዎች በግንባሩ ገጭቶ ባስቆጠራት ጎል ድሬዎች 1-0 በሆነ ዉጤት እየመሩ ወደ እረፍት አምርተዋል።
ከእረፍት መልስ ወልቂጤዎች ቅያሪ በማድረግ የኋላሸት ሰለሞንን ይዘዉ በመግባት ተጭነዉ ለመጫወት ቢሞክሩም በ53ኛዉ ደቂቃ ላይ የድሬዎች አማካይ ሱራፌል ጌታቸዉ ጎል አስቆጥሮባቸዉ ጨዋታው ወደ 2-0 አመራ።
ጨዋታዉ በ2-0 ዉጤት እስከ ጨዋታዉ መገባደጃ ድረስ ቢያመራም በ80ኛ ደቂቃ ላይ በወልቂጤዉ አጥቂ ጌታነህ ከበደ ላይ ጥፋት በመሰራቱ የተሰጠዉን የፍፁም ቅጣት ምት ኳስ እራሱ ጌታነህ ከበደ በመምታት ወደ ጎልነት ቀይሮ ጨዋታዉ 2-1 በሆነ ዉጤት ቀጥሏል።
ከጎሏ መቆጠር በኋላ በሁለቱም ቡድን በኩል የጎል ሙከራዎች ሳይስተዋሉ ጨዋታዉ በድሬዳዋ አሸናፊነት 2-1 በሆነ ዉጤት ተጠናቋል።
በዚህም መሰረት ድሬዳዋ ከተማ ይበልጥ ከወራጅ ቀጠና ከፍ በማለት ነጥቡን ወደ 33 በማድረስ 9ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።