የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የምድብ ለ የመጨረሻ ጨዋታ በዛሬዉ እለት በሻሸመኔ ከተማ እና በጂንካ ከተማ መሀከል ተካሂዶ ፍፃሜውን አግኝቷል።
ጨዋታዉን ሻሸመኔ ከተማ 2-1 በሆነ ዉጤት በማሸነፍ የ2015 ዓ.ም የከፍተኛ ሊግ ምድብ ለ ውድድርን በድል ቋጭቷል።
በዛሬዉ እለት በተካሄደዉ የምድብ ለ የፍፃሜ ጨዋታ ስነስርዓት ላይ አቶ ኢሳያስ ጂራ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽን ፕሬዝዳንት ፣ ዶ/ር ዳኛቸው ንገሩ የኢ/እ/ኳ/ፌ/ም/ፕሬዚዳንት ፣ የስራ አስፈፃሚ አባላቶች አቶ አዲሱ ቃሚሶ ፣ አቶ ሙራድ አብዲ እና አቶ ብዙአየው ጀምበሩ እንዲሁም የሲዳማ ክልል እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ አንበሴ አበበን ጨምሮ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን እና የሲዳማ ክልል እግር ኳስ ፌዴሬሽን እንዲሁም የሻሸመኔ ከተማ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
- ማሰታውቂያ -
ለውድድሩ መሳካት አስተዋጽኦ ላደረጉ ተቋማት፣ ግለሰቦች እና ተሳታፊ ክለቦች የሰርተፊኬት ስጦታ ከተበረከተ በኋላ በውድድሩ ሦስተኛ ለወጣዉ ቦዲቲ ከተማ የነሀስ ፣ ለንብ የብር እና ለአሸናፊው ሻሸመኔ ከተማ የወርቅ ሜዳሊያ ተበርክቷል። በማስከተል ውድድሩን ላሰናዳው ለሲዳማ ክልል እግር ኳስ ፌዴሬሽን የዋንጫ ሽልማት ተበርክቷል። እንዲሁም ለጉለሌ ክ/ከተማ የፀባይ ዋንጫ ሽልማት ተበርክቷል።
ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌድሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ ጂራ እና ለሲዳማ ክልል እግር ኳስ ፌድሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ አንበሴ አበበ የባህል አልባሳት ስጦታ የሻሸመኔ ከተማ አስተዳደር በስጦታ መልክ ያበረከተ ሲሆን በመጨረሻም ለአሸናፊው ሻሸመኔ ከተማ ዋንጫ ተበርክቶለት የእለቱ ስነ ስርዓቱ ፍፃሜውን አግኝቷል።