” እንደ አሰልጣኝ ውጤት ሲጠፋ ሶስተኛ ሰው ላይ ከማላከክ ሃላፊነት በመውሰድ ራሴን ከሀላፊነት
አግልያለሁ”
አሰልጣኝ ጸጋዬ ወንድሙ
/ ሻሸመኔ ከተማ/
በዘንድሮው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊን አንድም ነጥብ ማሳካት ያልቻለው የሻሸመኔ ከተማው አሰልጣኝ ጸጋዬ ወንድሙ ራሱን ከሃላፊነት ማንሳቱ ታውቋል።
- ማሰታውቂያ -
ትላንት በሲዳማ ቡና 3ለ1 የተሸነፈው ሻሸመኔ ከተማ በአራቱም ጨዋታዎች ተሸንፎ ምንም ነጥብ የሌለውና 5 የግብ ዕዳ ኖሮበት የሊጉ ግርጌ 16ኛ ደረጃ ላይ መገኘቱ አሰልጣኙን ለዚህ ውሳኔ የዳረገ እንደሆነ ይገመታል።
ውሳኔው አሰልጣኙ ቡድኑን ወደ ፕሪሚየር አሳድጎ ደጋፊውና የከተማው የስፖርት ማህበረሰብ ላይ ፈጥሮት የነበረው ደስታ ላይ ውሃ የቸለሰ ውሳኔ ነው ተብሏል። በርካቶች ሃላፊነትን በሚሸሹበት ሰበቡን በሌላ አካል ላይ በሚያላክኩበት የሀገሪቱ እግርኳስ አሰልጣኝ ጸጋዬ የኔ መልቀቅ መፍትሄ ከሆነ በሚል ሃላፊነት ወስዶ የስንብት ውሳኔ ሳይሰጠው የወሰደው የቅድሚያ ርምጃ ትኩረት የተቸረው ሆኗል።
በጉዳዩ ላይ አስተያየቱን የሰጠው አሰልጣኝ ጸጋዬ “ለነበረኝ ቆይታ አመሰግናለሁ ጥሩ ተስፋ የሚጣልበት ስብስብ ነው ያለን ነገር ግን ውጤት አልመጣም ይሄ ደግሞ ራሴን እንዳገል አድርጎኛል ደጋፊዎቻችን ይሄ አይገባቸውም በቀጣይ የሚደሰቱበት ውጤታማ ጊዜ እንዲገጥማቸው እመኛለሁ ” ብሏል።
ውሳኔህ የስንብት ስጋት ስላለብህ ይሆን..? ተብሎ የተጠየቀው አሰልጣኝ ጸጋዬ “በፍጹም ስጋት የለብኝም እነሱም እንድቆይ ይፈልጋሉ ባደረግነው ውይይት የተረዳሁትም ይሄ ነው ። እንደ አሰልጣኝ ውጤት ሲጠፋ ሶስተኛ ሰው ላይ ከማላከክ ግን ሃላፊነት በመውሰድ ራሴን አግልያለሁ” ሲል ተናግሯል።
ይህ የአሰልጣኝ ጸጋዬ ውሳኔ ከሊጉ ከሚገኙት 16 አሰልጣኞች ሃላፊነቱን የለቀቀ የመጀመሪያው አሰልጣኝ
አድርጎታል። በቀጣይም እንደተገመተው በተጠንቀቅ ከቆሙትና ክለብ አልባ ከነበሩት አሰልጣኞች መሃል ማን ይረከበው ይሆን የሚለው አጓጊ ሆኗል።