በአስራ አምስተኛዉ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የመጨረሻ ጨዋታ የቀን ዘጠኝ ሰዓት መርሐ ግብር ሀድያ ሆሳዕና እና ሀዋሳ ከተማ አንድ አቻ በሆነ ዉጤት ተለያይተዋል ።
ተመጣጣኝ በሚባል የጨዋታ እንቅስቃሴ የጀመረው የሁለቱ ክለቦች ፍልሚያ ገና በመባቻዉ ግብ ተቆጥሮበታል ፤ በዚህም በ9ነኛዉ ደቂቃ ላይ ከማዕዘን የተሻገረዉን ኳስ ቃልዓብ በጭንቅላቱ ለመለሰ አቀብሎት መለሰ በመቀስ ምት ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን ሀድያ ሆሳዕና መሪ ማድረግ ችሏል። ግብ ከተቆጠረባቸዉ በኋላ የአቻነት ግብ ለማግኘት በተደጋጋሚ ጫና መፍጠር የጀመሩት ሀዋሳ ከተማዎች በ25ተኛዉ ደቂቃ እዮብ አለማየሁ ከሳጥን ውጭ አክርሮ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ያሬድ በቀለ ኳሷን መልሶበታል።
በ35ተኛዉ ደቂቃ ላይ ሀዋሳ ከተማ የአቻነት ጎል አግኝተዋል ፤ በዚህም ከግራ በኩል የተገኘዉን ቅጣት ምት እዮብ አለማየሁ ሲያሻማ ከዚያም ተባረክ ሄፋሞ በጭንቅላቱ ሲገጭ ኳሱን ያገኘዉ ፀጋዓብ ዮሐንስ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን አቻ ማድረግ ችሏል። ከዚያም በኋላ በተመጣጣኝ የጨዋታ እንቅስቃሴ በቀጠለዉ የሀለቱ ክለቦች ጨዋታ ተጨማሪ ተጠቃሽ ሙከራ ሳይስተዋልበት አጋማሹ ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ ወዲያውኑ በ50ኛዉ ደቂቃ ላይ ሀድያ ሆሳዕናዎች ለግብ የቀረበ ሙከራ ማድረግ ችለዋል ፤ በዚህም ከማዕዘን ሳሙኤል ያሻገረዉን ኳስ ሰመረ ሀፍተይ በቀጥታ ወደ ግብ መቶት የነበረ ቢሆንም ኳሱ ለጥቂት በግቡ አናት ላይ ወጥቷል። ምንም እንኳን በጨዋታ ረገድ ብልጫ ቢወሰድባቸዉም አልፎ አልፎ በፊት መስመር ተጫዋቾቹ አሊ ሱለይማን እና እዮብ አለማየሁ አማካኝነት ተደጋጋሚ የሚባሉ ሙከራዎችን ማድረግ የቻሉት ሀይቆቹ ያን ያህል በቀሩት ደቂቃዎች ላይ አደጋ መፍጠር ሳይችሉ መርሐግብሩ አንድ አቻ በሆነ ዉጤት ተጠናቋል።
በዕለቱ ሁለተኛ መርሐግብር ድሬዳዋ ከተማ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አሳክቷል።
አመሻሽ 12 ሰዓት ሲል በጀመረው እና ተመጣጣኝ የሚባል የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ ባስመለከተን ጨዋታ ወልቂጤ ከተማዎች ከኋላ መስመር በሚላኩ ኳሶች አደጋዎችን ለመፍጠር ሲጥሩ በተቃራኒው ፤ ድሬዳዋ ከተማዎች በ12ተኛዉ ደቂቃ ላይ የተገኘዉን ቅጣት ምት በመሐመድ አማካኝነት በቀጥታ ወደ ግብ ቢሞክሩም ኳሷ ግን የግቡን ቋሚ ለትማ ለመልሳለች።
አልፎ አልፎ በሚገኙ አጋጣሚዎች ወደ ሶስተኛዉ የሜዳ ክፍል በመድረስ አደጋ ለመፍጠር ሲጥሩ የነበሩት ድሬዳዋ ከተማዎች በ30ኛዉ ደቂቃ ላይ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል ። በዚህም አጥቂዉ ቻርልስ ሙሴጌ ከሱራፌል ጌታቸዉ የተሻገረለትን ኳስ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
ምንም እንኳን ያን ያህል ተጠቃሽ ሙከራ ማድረግ አይቻሉ እንጅ አልፎ አልፎ በአቡበከር ሳኒ እንዲሁም ጋዲሳ መብራቴ አማካኝነት ሙከራዎችን ማድረግ ችለዉ የነበሩት ወልቂጤ ከተማዎች የአቻነት ግብ ሳያገኙ አጋማሹ ተጠናቋል።
ከመልበሻ ክፍል መልስ በርከት ያሉ ተጫዋቾችን ቀይረዉ ወደ ሜዳ በማስገባት የጨዋታዉን ብልጫ ለመዉሰድ ጥረት ማድረግ የቀጠሉት ሁለቱም ክለቦች እንደ መጀመሪያዉ አጋማሽ ሁሉ ሁለቱም ቡድኖች ይዘዉት የቀረቡትን የጨዋታ መንገድ ለመተግበር እና ግብ ለማስቆጠር ሲጥሩ የነበረ ቢሆንም ሁነቱ ሳይሳካ ጨዋታዉ በድሬዳዋ ከተማ 1ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።