በተጨዋችነት ለአማራ ውሃ ስራ፣ ለቴክስታይል፣ ለባህርዳር ከተማ ፣ ለባህርዳር ዩኒቨርስቲና ለጥቁር አባይ ተጫውቷል ። የ1ኛ ደረጃ ኮርሶችን የወሰደ ሲሆን ሲ. ቢ እና ኤ ላይሰንስ አግኝቷል.. በስልጠናውም አለም ባህርዳር ከተማ፣ ባህርዳር ዩኒቨርስቲ፣ በ2000 ሚሊኒየም በ25ቱ ክለቦች ጊዜ የተስፋዬ ኡርጌች ምክትል አሰልጣኝ ሆኖ ባህርዳር ዩኒቨርስቲን በፕሪሚየር ሊጉ ማሰልጠን ችሏል… የጥረት ሴቶችም ስልጠናውን አግኝተዋል… የአማራ ውሃ ስራዎች ድርጅትን ለአራት አመታት አሰልጥኖ ሁለት አመታትበተከታታይ የምድቡ ሻምፒዮን አድርጓቸዋል….ከሰምኑ ልደታ ክፍለ ከተማን ለማሰልጠን ከጫፍ የደረሰው እንግዳችን አሰልጣኝ እንዳወቀ አጥናፉ ከባልደረባችን ዮሴፍ ከፈለኝ ጋር አጠር ያለ ቆይታ አድርጓል…
ሀትሪክ:- የኤ ላይሰንስ ከወሰዳችሁ ቆያችሁ አይደል..?
እንዳወቀ: በርግጥ ቆይቷል…ተጨማሪ የማሻሻያ ኮርስ መውሰድ ነበረብን… ውጪ ወጥተን ስልጠና የማግኘት እድልም አላገጠመንም የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ይህን ማድረግ ነበረበት.. ያው ራሳችንን እያበቃን ግን እየታገልን እንገኛለን…
- ማሰታውቂያ -
ሀትሪክ:- እንደ አሰልጣኝ የሀገራችን እግርኳስ ላይ ተስፋ አለ ማለት ይቻላል..?
እንዳወቀ:- የሚታይ ብርሃንማ ነገር አለ… ግን ቀጣይነት ላይ ትንሽ ክፍተት አለ ግን ታዳጊ ላይ የተሻለ መሰራት አለብን እኔ ድሮ ስጫወት ከቤቴ ወጣ ስል ሜዳ ነበር አሁን ግን አንድም ሜዳ የለም ያ ትልቅ ጉዳት ነው መንግስት ኮንዶምኒየም ሲሰራ ይሄንን የሜዳ ጉዳይ ታሳቢ አለማድረጉ ቅር ያሰኛል ይሄ ጉዳት አለው
ሀትሪክ:- ብሄራዊ ቡድናችን ከሀገር ውጪ ወጥቶ መጫወቱ እንደ አሰልጣኝ ቅር አያሰኝም..?
እንዳወቀ:- በጣም ያማል ሳስበው ይከፋኛል ስደተኛ ቡድን መሆኑ በጣም ያስከፋል…120 ሚሊዮን ህዝብ ይዘን አንድም ደረጃውን የጠበቀ ሜዳ አለመኖሩ ያስከፋል። በየ ክልሉ የተጀመሩ ሜዳዎች ቢኖሩም አንዱንም አለመጨረስ ያበሳጫል ብሄራዊ በድን በሜዳው ቢጫወትኮ የደጋፊውን ጥቅም ያገኝ ነበር ውጤቱ ለመጥፋቱ አንዱ ምክንያት ከሜዳ ውጪ መሆኑ መታሰብ አለበት… ሜዳ አለመኖሩ ለመልካም ስማችን አይሆንም
ሀትሪክ:- ባህርዳር ዩኒቨርስቲ አለመኖሩ ምን ስሜት ይፈጥራል..?
እንዳወቀ:- ባህርዳር ዩኒቨርስቲ ምርጥና ታሪካዊ ክለብ ነበር አሁን ግን ፈርሷል… አንዳንዴ የሚመጡት የበላይ ጠባቂዎች እግር ኳስ ከወደዱ ክለቡም ይቆያል ካልወደዱ ይፈርሳል በነሱ እጅና ስሜት የሚወሰን መሆኑ ቅር ያሰኛል ይሄ መስተካከል አለበት ሙገር ሲሚንቶና ባህርዳር ዩኒቨርስቲ ምሳሌ ናቸው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተመልስ መምጣቱ ደስ ይላል እንጂ አጠቃላይ ሁኔታው መስተካከል አለበት ባይ ነኝ የኢትዮጵያ እግርኳስ ህልውና በከተማ አስተዳደር በላይ ጠባቂዎች መልካም ፍቃድ ላይ የተመሰረተ መሆኑ ቅር ያሰኛል።
ሀትሪክ:- የድሬዳዋ ከተማ ከንቲባ አቶ ከድር ለእግርኳስ ያላቸው ፍቅርስ ለየት አይልም..?
እንዳወቀ:- ከንቲባው ከድር ለብዙ ከንቲባዎች ሞዴል ነው የድሬዳዋ ከተማ ክለብን እየታደገ ነው ሜዳ እየሰራ ሀገርን እየጠቀመ ነው… የተሻለ የስራ አቅም ያለው ሰው ይመስለኛል ሌሎቹ ከሱ መማር አለባቸው ክለቦችም ከከንቲባው ተሞክሮ መውሰድ አለባቸው።
ሀትሪክ:- እስቲ ስለ ልደታ ከተማ እናውራ… ?
እንዳወቀ: ልደታ ከተማ በብሄራዊ ሊግ የሚወዳደር ክለብ ነው ከ20 ክለቦች 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል.. ከሰሞኑ ሲቪዬን አስገብቻለሁ እነሱን የማሰልጠን እድሉን እንደማገኝ ተስፋ አድርጋለሁ…. አውስኮድን ይዤ የምድቡ ሻምፒዮን በማድረጌ በልደታዎች እድል እንደማገኝ ተስፋ አደርጋለሁ… በ2013 እና በ2015 በተከታታይ ሻምፒዮን ሆኛለሁ… በ2014 ደግሞ በሀገራዊ ችግር የተነሳ ውድድሩ ተቋርጧል… ይህንን ከልደታ ጋር ማስቀጠል እፈልጋለሁ ልምዴም ይጠቅመኛል…
ሀትሪክ:- የመጨረሻ ጥያቄ…ለልደታ ከተማዎች የምትለው ነገር አለ..?
እንዳወቀ:-: ልደታዎች እድሉን ቢሰጡኝ ደስተኛ ነኝ ከመሪ ክለቦች ጋር ያለውን 12 ነጥብ ልዩነት የማጥበብ እድል ይኖረናል… የቡድኑን ጠንካራና ደካማ ጎን አይተን ለማረም ዝውውሩ ላይም ሁለትና ሶስት ተጨዋቾችን ጨምረን ወደ ዋንጫ ፉክክር ውስጥ የማስገባት አቅም አለኝ ብዬ አስባለሁ… ገና 19 ጨዋታ አለ ከምድቡ ሁለት ቡድን ስለሚያልፍ ከቻልኩ ሻምፒዮን ሆኜ ካልሆነ ቡድኑን ሁለተኛ አድርጌ ለመጨረስና ለማሳለፍ የምችለውን እንደማደርግ ልገልጽላቸው እፈልጋለሁ በአጠቃላይ ያለኝን የሻምፒዮንነት ልምድ ለልደታ ከተማዎች ማሳየት እፈልጋለሁ..