ሊጠናቀቅ የሁለት ሳምንታት ዕድሜ ብቻ በቀረዉ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ29ነኛ ሳምንት የመክፈቻ ዕለት የመጀመሪያ ጨዋታ ባህርዳር ከተማ ከሀዋሳ ከተማ ጋር መርሐግብራቸዉን አንድ አቻ በሆነ ዉጤት አገባደዋል።
ቀን ዘጠኝ ሰዓት ሲል በዋና ዳኛ ቢኒያም ወርቅአገኘሁ ፊሽካ በጀመረዉ የዕለቱ ቀዳሚ ጨዋታ ሁለቱም ክለቦች ተመጣጣኝ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴን እያስመለከቱን ጅማሮ ቢያደርጉም ፤ ገና በጊዜ ግን ማለትም በአስረኛዉ ደቂቃ ላይ የጣና ሞገዶቹ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል ። በዚህም በተጠቀሰዉ ደቂቃ የአብስራ ተስፋየ ወደ ሳጥን ያሻገራትን ኳስ የሀዋሳዉ ተከላካይ ሰለሞን ወዴሳ ኳሷን በዕጅ መንካቱን ተከትሎ የተሰጠዉን ፍፁም ቅጣት ምት አምበሉ ፍቅረሚካኤል አለሙ ወደ ግብነት መቀየር ችሏል።
ከግቧ መቆጠር በኋላ በተደጋጋሚ በፊት መስመር ተጫዋቾቹ የመስመር ላይ ማጥቃት አደጋ ለመፍጠር ይጥሩ የነበሩት ባህርዳር ከተማዎች በፍራኦል መንግስቱ እና ፍቅረሚካኤል አማካኝነት የተወሰኑ አጋጣሚዎችን ቢያገኙም ነገር ግን መጠቀም ሳይችሉ ሲቀሩ ፤ ገና በጊዜ ግብ የተቆጠረባቸዉ ሀይቆቹም በመልሶ ማጥቃት የአቻነት ግብ ለማግኘት ያደረጉት ጥረት ከዕረፍት በፊት ሳይሳካ ቀርቶ አጋማሹ በባህርዳር መሪነት ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ እዮብ አለማየሁን እና ቸርነት አውሽን በሌሎች ተጫዋቾች ቀይረዉ በማስወጣት የማጥቃት ቅርፃቸዉን ለመቀየር ጥረት ያደረጉት ሀዋሳ ከተማዎች ምንም እንኳን በእንቅስቃሴ ረገድ የተለየ ነገር ማስመልከት ባይችሉም ከብዙ ጥረት በኋላ በ79ነኛዉ ደቂቃ ላይ በአጥቂዉ አሊ ሱለይማን የፍፁም ቅጣት ምት ግብ አማካኝነት የአቻነት ግብ አስቆጥረዉ መርሐግብራቸዉን አንድ አቻ በሆነ ዉጤት ፈፅመዋል።
በዕለቱ ሁለተኛ መርሐግብር ሲዳማ ቡና ድሬዳዋ ከተማን ሁለት ለዜሮ በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
በዋና ዳኛ ሚካኤል ጣዕመ መሪነት አመሻሽ 12:00 ሰዓት በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ገና በጊዜ ሲዳማ ቡናዎች ጨዋታዉን መምራት የጀመሩበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም በአምስተኛዉ ደቂቃ ላይ ከወደ ግራ መስመር በኩል ከቅጣት ምት የተሻማዉ ኳስ የግቡን ቋሚ ገጭቶ ሲመለስ ኳሱን ያገኘው ኢማኑኤል ላሪየ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን ሲዳማ ቡና መሪ ማድረግ ችሏል።
ከዚች ግብ መቆጠር ከአራት ደቂቃዎች በኋላ በ9ነኛዉ ደቂቃ ላይ ደግሞ ቶሎ ቶሎ ወደ ድሬዳዋ የግብ ክልል መድረስ የቻሉት ሲዳማ ቡናዎች በድጋሚ ሁለተኛ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም ከቀኝ በኩል የተገኘዉን የቅጣት ምት ኳስ የሲዳማዉ አምበል ደስታ ደሙ በቀጥታ ወደ ግብነት ቀይሮ መሪነታቸዉን ወደ ሁለት ለዜሮ ከፍ ማድረግ ችለዋል።
ገና በጊዜ ተከታታይ ጎሎች የተቆጠሩባቸዉ ድሬዳዋ ከተማዎች ወደ ጨዋታዉ ለመግባት በኳስ ቁጥጥሩ ተሽለዉ ሲንቀሳቀሱ የተመለከትናቸው ቢሆንም ነገር ግን የሚገኙ ዕድሎችን ወደ ግብነት በመቀየርም ሆነ ስል በመሆን ረገድ ግን ደካማ ሁነዉ ተስተዉሏል። በተቃራኒው ጨዋታዉን በመምራት ላይ የነበሩት ሲዳማ ቡናዎች በቀሪ የጨዋታዉ ደቂቃዎች በተደጋጋሚ ድንቅ የሚባሉ ዕድሎችን አግኝተዉ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን በመጠቀሙ ረገድ እየተዳከሙ ቀጥለዋል። ይህንን ተከትሎም ሁለቱም ክለቦች ተጨማሪ ግብም ሆነ የአቻነት ግብ ለማግኘት ያደረጉት ጥረት ፍሬ ሳያፈራ ቀርቶ መርሐግብሩ ጥሩ በነበረዉ በሲዳማ ቡና ሁለት ለዜሮ አሸናፊነት ተጠናቋል።