በዋና ዳኛ ሙሉቀን ያረጋል ፊሽካ ቀን ዘጠኝ ሰዓት ሲል በጀመረዉ የዕለቱ ብቸኛ ጨዋታ ባሳለፍነዉ ሳምንት ከተከታታይ ሰባት ሳምንታት ያለመሸነፍ ጉዞ በኋላ ለኢትዮጵያ ቡና ዕጅ የሰጠዉ ኢትዮጵያ መድን በመጀመሪያዎቹ ደቂቃዎች ላይ በንፅፅር የተሻለ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ ያስመለከተን ቢሆንም ነገር ግን ዕድሎችን በመፍጠር እና ጫናዎችን በመፍጠር ረገድ ግን ደካማ ሁነዉ ተመልክተናቸዋል።
በተመሳሳይ ቀዝቃዛ በነበረዉ የሁለቱ ክለቦች የዕለቱ ጨዋታ በመከላከል ጥንካሬያቸዉ የሚታወቁት ሀድያ ሆሳዕናዎች በአብዝሀኛዉ የጨዋታዉ ክፍለ ጊዜ የመጀመሪያ አጋማሽ ተቀዳሚ ተግባራቸዉን መከላከል አድርገዉ አልፎ አልፎ ደግሞ በሚገኙ የመልሶ ማጥቃት እና የመስመር ላይ ማጥቃት ሂደቶች አደጋ ለመፍጠር ሲጥሩ የተስተዋለ ቢሆንም ነገር ግን ሁለቱም ክለቦች ያን ያህል ተጠቃሽ ሙከራ ማድረግ ሳይችሉ እና ግብም ማስቆጠር ሳይችሉ የመጀመሪያው አጋማሽ ፍፃሜዉን አግኝቷል።
ከዕረፍት መልስ በተመሳሳይ እንቅስቃሴ በቀጠለዉ ጨዋታዉ አሁንም ክለቦቹ ወጥ የሆነ ብቃትን ማስመልከት ተስኗቸዉ የተመለከትን ሲሆን ፤ በተደጋጋሚ ከሚደረጉ ሁለት እና ሶስት የሚቆራረጡ ቅብብሎች በዘለለ ለተመልካች ሳቢ ያልሆነ እንቀስቃሴን ሲያሳዩ የነበረ ቢሆንም ጨዋታዉ ሊጠናቀቅ ዘጠኝ ደቂቃ ሲቀረዉ ግን ሳጥን ውስጥ ወገኔ ገዛኸኝ ከብሩክ የቀበለዉን ኳስ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡ ኢትዮጵያ መድን ጨዋታዉን አንድ ለዜሮ እንዲያሸንፍ አስችሏል።