ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ/ባንኮች
ስም ፡ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ/
ባንኮች ስፖርት ክለብ
ምስረታ ፡ 1975 ዓ/ም
ዋና አሰልጣኝ ፡–ፀጋዩ ኪዳነ ማሪያም
ም/አሰልጣኝ ፡– ሲሳይ ከበደ
የህክምና ባለሙያ ፡– ትዛዙ አስፋው
የበረኛ አሰልጣኝ ፡– ንጉሴ ወልደ አማኑኤል
አምበል ፡ መላከ መስፍን
ኢትዮጵያ ባንኮች ስፖርት ክለብ በሠባት ባንኮች ባለቤትነት የሚተዳደር የስፖርት ክለብ ነው፡፡ በእግር ኳሱ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ እየተሳተፈ ሲሆን በጥሎ ማለፍ ሻምፒዮን ባመጣው ውጤት ሁለት ጊዜ በአፍሪካ ኮንፌዴርሽን ዋንጫ የመሣተፍ እድል አግኝቷል፡፡
ምስረታ
ኢትዮጵያ ባንኮች ስፖርት ክለብ የተመሰረተው በ 1975 ዓ/ም በአራት ባንኮች ባለቤትነት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ፣ ንግድ ባንክ፣ ልማት ባንክ እና ኮንስትራክሽንና ቢዝነስ ባንክ ናቸው፡፡ በወቅቱ በሀገሪቱ የሚንቀሳቀሱ ባንኮች እነዚህ ብቻ ነበሩ በ 1995 ዓ/ም በአዲስ መልክ ሲጠናከር ሦስት የግል ባንኮች ድጋፍ በማድረግ ተቀላቀሉ፡፡ ወጋገን፣ ንብ እና አዋሽ ባንክ ናቸው እናም በአሁኑ ወቅት ሠባት ባንኮች በሚያዋጡት ገንዘብ የሚቀሳቀስ ስፖርት ክለብ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ባንኮች ከምስረታው በኃላ በኢትዮጵያ ሻምፒዮና ላይ ተሳትፏል፡፡ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሲጀመርም ከሊጉ መስራች ክለቦች አንዱ ነው፡፡ እስካሁን ወደ ታችኛው ዲቪዚዬን አልወረደም ዋንጫም አላነሳም ከ 1992-1994 በተከታታይ ለሦስት አመታት አራተኛ ደረጃን ያገኘበት ውጤት የሊጉ የተሻለው ሆኖ ተመዝግቦለታል፡፡
በጥሎ ማለፍ ደግሞ የተሻለ ሪከርድ አለው፡፡ በ 1996 ኢትዮጵያ ቡናን 1ለ0 በማሸነፍ የጥሎ ማለፍ ሻምፒዮን ሆነ፡፡ በአሸፊዎች አሸናፊ ዋንጫም የፕሪሚየር ሊጉ ሻምፒዮን የነበረውን ሀዋሳ ከነማን ለማሸነፍ ሁለተኛ ዋንጫ አግኝቷል፡፡ በ 2001 ዓ/ም በጥሎ ማለፉ ለፍፃሜ ደርሶ በቅዱስ ጊዮርጊስ ተሸንፎ ዋንጫ ቢያጣም የሚያፅናናው ነገር አግኝቶ ነበር፡፡ ቅ/ጊዮርጊስ የፕሪሚየር ሊጉ ሻምፒዮን በመሆኑ በአፍሪካ ሻምፒየንስ ሊግ ይሳተፍ ነበር፡፡ እናም በኮንፈዴሬሽን ዋንጫ የመሳተፍ እድሉ ለፍፃሜ ተፋላሚው ባንኮች ተሰጥቷል፡፡
ባንኮች በኢንተርናሽናል
ኢትዮጵያ ባንኮች ሁለት ጊዜ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ዋንጫ የመሣተፍ እድል አግኝቷል፡፡ የመጀመሪያው 1998 [2005] ነው በመጀመሪያው ዙር ከኬንያው ሼሚልል ሹገር ጋር ቢገናኝም ተጋጣሚው ራሱን በማግለሉ ወደ መጀመሪያው ዙር ያልፋል በአንደኛው ዙር ከግብፅ ሞካውሉን ጋር የተገናኘ ሲሆን አዲስ አበባ ላይ ያለ ግብ ተለያይቶ ግብፅ ላይ 3 ለ 1 ተሸንፎ ከውድድሩ ተሰናብቷል፡፡ ሁለተኛው የተሳትፎ እድል ያገኘው በ 2002 ዓ/ም ነው፡፡ በቅድመ ማጣሪያው ከኬንያው ሊያፓርድ ጋር ተገናኘ ናይሮቢ ላይ 3 ለ 1 ተሸንፎ ቢመለስም አዲስ አበባ ላይ 3 ለ 0 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር አልፏል፡፡ በአንደኛው ዙር ከግብፅ ሀራስ ኤልሀዱድ አልሃዲድ ጋር ተገናኘ፡፡ አዲስ አበባ ላይ አንድ አቻ ከተለያዩ በኃላ በአሌክሳንደሪያው የመልስ ጨዋታ ግን ያልታሰበ ሽንፈት ደረሰብ 5 ለ 0 በሆነ ሰፊ ውጤት ተሸንፎ ከውድድሩ ውጭ ሆነ፡፡