የፌደሬሽኑ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት ማሟያ ምርጫም ተከናውኗል !
በአፍሪካ ህብረት መሰብሰቢያ አዳራሽ የተካሄደዉ 15ተኛዉ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በክቡር ፕሬዝደንቱ አቶ ኢሳያስ ጅራ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር የተጀመረ ሲሆን በንግግራቸውም :-
🔸 ካስተላለፉት የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ባሻገር የሰሯቸዉን በጎ ተግባራት ያብራሩ ሲሆን ውድድሮችን ከመከወን አንፃር ፣ ለአሰልጣኞች የካፍ ስልጠና ከማሰጠት አንፃር ፣ ከሜዳ ዉጭ በሚደረጉ ጨዋታዎች የብሔራዊ ቡድኑ ወጪዎች በተለያዩ አካላት እንዲሸፈኑ መደረጉን ፣ የሴቶች ውድድር ላይ ጥራቱ እንዲጨምር ፌደሬሽኑ በራሱ ወጪ እያወጣ ሲደግፍ እንደነበር የገለፁ ሲሆን ፤
🔸 በተጨማሪም ለወንዶች በእግርኳሱ ዘርፍ ብዙ ብር እየወጣ ለሴቶች አለመዉጣቱ ከዚህ በኋላ ሊቆም እንደሚገባ ፣ ከሜዳ ውጭ መጫወታቸው ችግር እንደሆነባቸው በዚህም መንግስት በፋይናንስ ሊደግፋቸዉ እንደሚገባ ሲገልፁ በመጨረሻም ለብሔራዊ ቡድኑ ከመንግስት የሚለቀቀዉ ገንዘብ ድጋፍ የሚለዉ ቀርቶ በጀት መሆን እንዳለበት እና የትግራይ ክልል እግርኳስ ወደነበረበት እንዲመለስ ሁሉም እንዲጥር መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
- ማሰታውቂያ -
– ከክቡር ፕሬዝዳንቱ የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር በኋላም የዕለቱ የክብር ዕንግዳ የባህል እና ስፖርት ሚኒስተር ሚኒስር ዲኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት በተመሳሳይ ንግግር አድርገዉ የ2015 አመት የበጀት እቅድ አፈፃፀም ሪፖርት በዋና ፀሀፊዉ አቶ ባህሩ ጥላሁን አማካኝነት ቀርቧል።
🔹 በዚህም አጠቃላይ በዓመቱ የተከናወኑ ተግባራትን በዝርዝር ለጉባኤያተኛዉ ያቀረቡ ሲሆኑ ከነዛም መካከል :- በአመቱ ለሚቀጥሉት አራት አመታት የሚመሩ አመራሮች ምርጫ መካሄዱን ፣ በተለያዩ የዕድሜ ዕርከኖች ያሉ የሴት እና የወንድ ብሔራዊ ቡድኖችን በማጣሪያ ውድድሮች ማሳተፍ ፣ የወዳጅነት ጨዋታዎችን ብሔራዊ ቡድኑ በበቂ ሁኔታ እንዲያገኝ ማድረግ መቻሉን ፤ በእግርኳስ ዙሪያ አገልግሎት የሚሰጡ ባለሙያዎችን እና አመራሮችን ማፍራት ፣ በፌደሬሽን ደረጃም ኤሊት ኢንተርናሽናል ዳኞች በቂ ስልጠና እንዲያገኙ እና በዚህም 21 ለሚሆኑ እንተርናሽናል ዳኞች ስልጠና መሰጠቱን በተጨማሪም ለ385 ዳኞች በተለያዩ ክልሎች ስልጠና መሰጠቱ ተገልጿል።
🔹 ከዚህ በተጨማሪም በግንባታ ላይ ላሉ ስታዲየሞች የመፍትሔ አካል ለመሆን መሞከሩን ፣ የፌደሬሽኑ የአደረጃጀት የሰዉ ሀይልና አሰራር ስርዓቱን ምቹ ለማድረግ መሞከሩ ፣ የተለያዩ አገር አቀፍ ውድድሮችን በተቻለ መጠን ለማካሄድ መሞከሩን ፣ ክለቦች ዓለም አቀፍ የእግርኳስ ማህበር ያወጣዉን የላይሰንስ ስርዓት መሰረት አድርገዉ እንዲደራጁ ለማድረግ መሞከሩን ፣ የስፖርት ህክምና አገልግሎቶችን ማሻሻል እንዲሁም በየደረጃዉ ካሉ የፌደሬሽኑ አጋር አካላት ጋር ያሉ ግኑኝነቶችን ማጠናከር ላይ እና መሰል ዝርዝር የነበሩ ጉዳዮች በሪፖርቱ ላይ ውይይት ተደርጎባቸዉ ጉባኤዉ ለምሳ ተበትኗል።
🔸ከምሳ በኋላም በከሰዓቱ የጉባኤዉ ቆይታ መባቻ በአቶ ነብዩ አማካኝነት አጠቃላይ የፋይናንስ ሪፖርት የቀርበ ሲሆን ፤ ለውድድሮች ፣ ለብሔራዊ ቡድን እና ለሌሎች ወጪዎች እንዲሁም ገቢዎችን በተመለከተ አጠቃላይ ሪፖርት ቀርቦ ገባኤያተኛዉ ውይይት አድርጎበት ፀድቋል። ይህ በእንዲህ እንዳለም የኦዲት ሪፖርቱ ቀርቦ በተመሳሳይ በ122 ድምፅ የፀደቀ ሲሆን ከቤቱ ለተነሱ ጥያቄዎች ፕሬዚደንቱ ምላሽ ሰጥተዉበታል።
🔸 በመቀጠል የፌደሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ኢሳያስ ጅራ ጉባኤያተኛዉን በማስፈቀድ በአሁኑ ሰዓት ህመም ላይ ስለሚገኘዉ አስራት ሀይሌን የተመለከተ ቪዲዮ ለዕይታ እንዲቀርብ ያደረጉ ሲሆን ፤ በአዳራሹ ያሉት በሙሉም ለአስራት ህክምና የበኩላቸዉን እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።
🔸 በመጨረሻም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት የማሟያ ምርጫ ተከናዉኖ አሸናፊዎች ታውቀዋል ፤ በዚህም :-
1. ኮ/ል አወል አብዱራሂም (ከትግራይ ክልል) – 92 ድምፅ
3. አቶ ኢብራሂም ሙክታር (ከአፋር ክልል) – 80 ድምፅ
4. አቶ ማዕረጉ ሀብተማርያም (ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ)- 76 ድምፅ ሆነዉ ተመርጠዋል።
በመጨረሻም ጉባኤዉ ላይ የምርጫ ረቂቅ ደንብ ቀርቦ ውይይት ከተደረገበት በኋላ ፀድቆ ፤ ጉባዔውም በአቶ ኢሳያስ ጅራ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የመዝጊያ ንግግር ፍፃሜውን አግኝቷል።