“ከክላውድ አውት ኩባንያ ብዙ ውጤታማ የሆነ ሥራ እንጠብቃለን። ቢሮክራሲው እንዳያስቸግረውም የቻልነውን ሁሉ እንጥራለን”
አቶ ባህሩ ጥላሁን
/የፌዴሬሽኑ ዋና ስራ አስፈጻሚ/
“አሰልጣኞች፣ዳኞችና ታዳጊዎች ስልጠና እንዲያገኙ የእኔ ሥራ ድልድይ መፍጠር ነው”
አቶ ዮሀንስ ዘውዱ
/የክላውድ አውት ኩባንያ ዋና ስራ አስኪያጅ/
የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ከክላውድ አውት ኩባንያ ብዙ ውጤታማ ሥራ እንደሚጠብቅ ለዚህም ቢሮክራሲው እንዳያስቸግረው የቻለውን ሁሉ እንደሚያደርግ አስታወቀ።
- ማሰታውቂያ -
የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ከክላውድ አውት ኩባንያ ጋር አብሮ ለመስራት ስለተስማማበት ስምምነት የፌዴሬሽኑ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ባህሩ ጥላሁንና የኩባንያው ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ዮሀንስ ዘውዱ/ ጆኒ ቬጋስ / በጋራ በፌዴሬሽኑ ጽ/ ቤት በሰጡት መግለጫ የሁለቱ ተቋማት ስምምነት ለኢትዮጵያ እግር ኳስ እድገት ትርጉም ያለው እንደሆነ አስረድተዋል።
“የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን የማይደርስባቸው አድማሶች አሉ። ሁሉንም ቦታ መድረስ አንችልም ወይም ሁሉንም የምናውቅ የተዋጣልን አይደለንም ስለዚህ አብረውን የሚሠሩ አጋሮች ያስፈልጉናል” ያሉት ዋና ስራ አስፈጻሚው ” ዮሐንስ ዘውዱ በክላውድ አውት ኩባንያው ከትላልቅ ካምፓኒዎች ጋር ያደረጋቸው ግንኙነቶች አሉ። እነዚህን ካምፓኒዎች ለማግኘት እጅግ በጣም ከባድ እንደሆነ እናውቃለን… እሱ ደግሞ ትውልደ ኢትዮጵያዊ በመሆኑ ለሀገሩ አስተዋጽኦ ማድረግ ይፈልጋል በስምምነቱም ተደስተናል” ሲሉ አስረድተዋል።
ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ ባህሩ “አቶ ዮሀንስ ጊዜውን የሚያሳልፈው ኮከብ ከሆኑ ተጫዋቾች ጋር እንደሆነ ይታወቃል እና እኛ የምንፈልገው ነገር አለ እሱም ለሀገሩ መሥራት የሚፈልገው ነገር አለ ስለዚህ አብረን መሄዱን መርጠናል። ከዕቅዳችን አንዱ ዱባይ በሚገኘው ቢሮው አማካይነት በታዳጊ ስልጠና ዘርፍ ከሳውዲ አረቢያ ጋር ያለውን ጠንካራ የሆነ መንግሥታዊ ትስስር በእግርኳሱም ለማምጣት ምቹ ሁኔታ ይፈጥርልናል ብለን እናምናለንሲሉ አብራርተዋል።
“ከቀድሞዎቹ ፍራንሲስኮ ቶቲ፣ ባካሪ ሳኛና አሁን ደግሞ እነ ሳካን ጨምሮ በርካታ ኮከቦችን በቀላሉ የሚያገኝ ሰው ነው። ካምፓኒውም በዛ ደረጃ የሚሠራ ነው። ከተቋሙ ብዙ ውጤታማ የሆነ ሥራ እንጠብቃለን። ቢሮክራሲው እንዳያስቸግረውም የቻልነውን ሁሉ እንጥራለን” ያሉት አቶ ባህሩ ” ከካፍና ፊፋ ጋር ያለን ግንኙነት ብቻውን በቂ አይደለም ዮሐንስ ዘውዱ ታላላቅ የእግርኳስ ሰዎች እና ክለቦች ጋር አለም አቀፍ ሥራዎችን እንደሚሠራ ይታወቃል። ለኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ይዞት የመጣው ሥራ ቀላል አይደለም” ሲሉ ስምምነቱን አወድሰዋል።
በስምምነቱ መሰረት አቶ ዮሀንስና ተቋማቸው ልክ እንደ ኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን በመሆን ከተለያዩ የአለማችን ታላላቅ ሊጎች ጋር እና የስፖርት ትጥቅ አምራቾች ጋርም ሆነ ሌሎች ፌዴሬሽኖች ጋር በጋራ በመሆን የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽንን በመወከል ለኢትዮጵያ እግርኳስ የሚጠቅመውን እንዲያመጡ
ተቋማዊ ውክልና እንደተሰጠው ተናግረዋል።
የተቋሙ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ዮሀንስ ዘውዱ በበኩላቸው “የእኔ ሥራዬ ድልድይ መፍጠር ነው በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽንና የውጭ ሊጎች መሃል መልካም ግንኙነት በመፍጠር የኢትዮጵያን እግርኳስ ፌዴሬሽን ወደ ላይ አውጥቶ ዕውቅና ለመስጠት፣ የወዳጅነት ጨዋታዎችን ለማድረግ፣ ለሀገራችን አሰልጣኞችና ዳኞች የስልጠና ግንኙነቶችን ለማመቻቸትና ከውጪው ዓለም ጋር በምንፈጥረው ግንኙነት ታዳጊዎችን የማፍራት ሥራ ለመስራት ነው። ክላውድ አውት ፌዴሬሽኑ ወደ ውጪ ጉዞ ሲያደርግ ከሆቴሎች ጋር መልካም ግንኙነት ለመፍጠርና ወጪውን ለመቀነስ ዋና አላማው እድርጎ ይንቀሳቀሳል” ሲል ተናግረዋል። አቶ ዮሀንስ ከዚህ ቀደም የተጫዋቾችን የዕረፍት ጊዜ እጅግ ምቹ በሆነ ሁኔታ ያዘጋጁ እንደነበር በማስረዳት አሁን እነሮሜሎ ሉካኩ ከቀድሞዎቹ ደግሞ ደግሞ ባካሪ ሳኛን የመሳሰሉ ተጫዋቾች ከካምፓኒያቸው ጋር እንደሚሠሩ ጠቁመዋል።
ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ ባህሩ በሁለቱ ወገኖች መሃል ለፈጠረው የግንኙነት መስመር ጋዜጠኛ መንሱር አብዱልቀኒን አመስግነዋል።