ከሁለት ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ በሀያኛዉ ሳምንት የሊጉ መርሐግብር ኢትዮ ኤሌትሪክን በመርታት ወደ ድል ተመልሰዉ የነበሩት አዳማ ከተማዎች ምሽት ላይ በተደረገዉ የ21ኛዉ ሳምንት መርሐግብር በወራጅ ቀጠናዉ ላይ የሚገኘዉን ሲዳማ ቡና 3ለ1 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችለዋል።
ከጨዋታዉ የመጀመሪያ ደቂቃ አንስቶ የኳስ ቁጥጥር የበላይነቱን በመዉሰድ ተጋጣሚ ቡድን ላይ ገና በጊዜ ጫና ማሳደር የጀመሩት አዳማዎች በጨዋታው መባቻ ላይ በ7ተኛዉ ደቂቃ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም የፊት መስመር ተጫዋቹ አድናን ረሻድ ከአዳማ የቀኝ ማጥቃት በኩል ከዮሴፍ ታረቀኝ የተቀበለዉን ኳስ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ከግቧ መቆጠር በኋላም አዳማዎች የሜዳዉ መሐል ክፍል ላይ በቁጥር በርከት ብለዉ በመገኘት በአንድ ሁለት ቅብብል አልፎ አልፎም በመስመር በኩል ተጨማሪ ግብ ለማግኘት ሲጥሩ በተቃራኒው በግዜ ግብ የተቆጠረባቸዉ ሲዳማዎች ደግሞ በሁለቱ የመስመር ተጫዋቾቻቸው በኩል ግብ ለማስቆጠር ሲጥሩ ተስተውሏል።
ተደጋጋሚ ጊዜ የአዳማ ከተማ የግብ ክልል ውስጥ ቢደርሱም የአቻነት ግብ ለማስቆጠር ግን ሲቸገሩ የነበሩት እና ሳጥን ዉስጥ አይናፋር የነበሩት ሲዳማዎች መደበኛዉ 45 ደቂቃ ተጠናቆ በጭማሪ ሰዓት ላይ ሁለተኛ ግብ አስተናግደዋል። በዚህም የመሐል ሜዳዉ ተጫዋች አማኑኤል ጉበና ከመስዑድ የተቀበለዉን ኳስ በቀጥታ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡ አጋማሹን ሁለት ለዜሮ እየመራ ወደ መልበሻ ክፍል እንዲያመሩ ማድረግ ችሏል።
ከዕረፍት መልስ አሁንም የማጥቃት ሀይላቸዉን አጠንክረዉ ወደ ሜዳ የተመለሱት አዳማዎች ከተደጋጋሚ ሙከራዎች በኋላ ሶስተኛ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም በ64ተኛዉ ደቂቃ ላይ አሜ መሐመድ ላይ ጥፋት መሰራቱን ተከትሎ በአዳማ የግራ ማጥቃት በኩል የተገኘዉን ቅጣት ምት ወጣቱ የመስመር ተጫዋች ዮሴፍ ታረቀኝ ወደ ግብነት በመቀየር የክለቡን መሪነት ወደ ሶስት ከፍ ማድረግ ችሏል።
ሶስተኛ ግብ ከተቆጠረባቸዉ በኋላ ወደ ጨዋታዉ የሚመልሳቸዉን ግብ ለማስቆጠር በርከት ያሉ የማጥቃት ባህሪ ያላቸዉን ተጫዋቾች ቀይረዉ ወደ ሜዳ ማስገባት የቻሉት ሲዳማዎች ከአስር ደቂቃዎች በኋላ በ74ተኛዉ ደቂቃ ላይ በፊት መስመር ተጫዋቹ አቤል እንዳለ አማካኝነት የማስተሳዘኛ ግብ ማግኘት ችለዋል። በቀሪ ደቂቃዎች ሁለቱም ክለቦች ጥሩ ጥሩ የሚባሉ ለግብ የቀረቡ መከራዎችን ማድረግ ቢችሉም በጨዋታው ተጨማሪ ግብ ሳይስተናገድበት በአዳማ ከተማ 3ለ1 አሸናፊነት ተጠናቋል።
ዉጤቱን ተከትሎም ተከታታይ ድል ያስመዘገበዉ አዳማ ከተማ በ30 ነጥቦች ስድስተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ በተቃራኒው በምሽቱ ጨዋታ ሽንፈት የገጠመዉ ሲዳማ ቡና ደግሞ በ21 ነጥቦች አስራ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።