”በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ካፕ ዛማሌክ ላይ ያስቀጠርኩት ጎል በህይወቴ ትልቁን የስኬት ደረጃ ይዟል”
”ኢትዮጵያዊ ተጫዋች ሆነህ የብሄራዊ ቡድን ማለያ ከመልበስ በላይ የሚያስደስት ነገር የለም”
”ከ15 ዓመት በኋላ በሊጉ ለሻሸመኔ ከተማ የመጀመሪያ ጎል ያስቀጠርኩ ታሪካዊ ተጫዋች በመሆኔ ኩራት ይሰማኛል” ያሬድ ዳዊት /የሻሸመኔ ከተማ ተጫዋች/
ትዉልድ እድገቱን በወላይታ ሶዶ ከተማ በማድረግ እግር ኳስን በሰፈር እና በትምህርት ቤት እየተጫወተ ጀምሮ ከአለኝታ ፕሮጀክት አንስቶ እስከ ሀገራችን ትልቁ የዉድድር እርከን በሆነዉ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በመጫወት በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ካፕ ላይ ጎል ማስቆጠር ከቻለዉ እና የሻሸመኔ ከተማን የሊጉ ተሳትፎን የመጀመሪያ ጎል ካስቆጠረዉ በአሁን ጊዜ ለሻሸመኔ ከተማ በመጫወት ላይ ከሚገኘዉ ያሬድ ዳዊት ጋር የሀትሪክ ስፖርት ድህረገጽ ጋዜጠኛ የሆነዉ ብሩክ ሐንቻቻ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የሚከተለዉን ቃለ መጠየቅ አድርጓል።
- ማሰታውቂያ -
ሀትሪክ :- በመጀመሪያ ራስህን ለሀትሪክ ቤተሰቦች አስተዋውቅልን ?
ያሬድ :- ያሬድ ዳዊት እባላለሁ።
ሀትሪክ :- ያሬድ የት ተወልዶ አደገ ? ለቤተሰቡስ ስንተኛ ልጅ ነዉ ?
ያሬድ :- ተወልጄ ያደኩት በወላይታ ሶዶ ከተማ ሲሆን ለቤተሰቤ የመጀመሪያ ልጅ ነኝ።
ሀትሪክ :- እግር ኳስን የጀመርክበትን አጋጣሚ አጫዉተን ?
ያሬድ :- እግር ኳስን ሰፈር እና ትምህርት ቤት በመጫወት ነበር የጀመርኩት።
ሀትሪክ :- መጀመሪያ የት ነበር የተጫወትከዉ ?
ያሬድ :- በመጀመሪያ የተጫወትኩት በወላይታ ሶዶ አለኝታ በተሰኘ የእግር ኳስ ፕሮጀክት ቡድን ዉስጥ ነበር።
ሀትሪክ :- ከእዛ ቀጥለህስ በስንት አመተ ምህረት የት የት ተጫወትክ ?
ያሬድ :- ከእዛ በመቀጠል 2006 ዓ.ም የወላይታ ዲቻ B ቡድንን የተቀላቀልኩ ሲሆን ከእዛን 2008 ወደ ዋናዉ ቡድን በማደግ እስከ 2015 ድረስ በወላይታ ዲቻ ተጫዉቻለዉ።
ሀትሪክ :- በእነዛ ክለቦች የነበረህን ቆይታ አጫዉተን
ያሬድ :- በፕሮጀክትም በወላይታ ዲቻም ጥሩ የሚባል ቆይታ አሳልፌያለሁ በእነዛ አመታት ከወላይታ ዲቻ ጋር የጥሎ ማለፍ ዋንጫ አሳክቻለሁ እንዲሁም በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ካፕም ጥሩ የሚባል ቆይታ አሳልፍያለሁ።
ሀትሪክ :- ወደ ሻሸመኔ ከተማ የመጣህበትን አጋጣሚ አጫዉተን። በስንት አመተ ምህረት መጣህ ?
ያሬድ :- ሻሸመኔ ከተማን ዘንድሮ የተቀላቀልኩ ሲሆን በአሰልጣኝ ፀጋዬ ወንድሙ ጥሪ ቀርቦልኝ ጥሪዉን በመቀበል ተቀላቅያለሁ።
ሀትሪክ :- እስካሁን ድረስ በሻሸመኔ ከተማ ቤት እያሳለፍክ ስለምትገኘዉ ቆይታ አጫዉተን ?
ያሬድ :- እንደ አጀማመር በዉጤት ደረጃ ጥሩ ባንሆንም በእንቅስቃሴ ደረጃ ግን ለወደፊቱ ተስፋ የሚሰጥ ጥሩ እንቅስቃሴ አለ። ያን ነገር ደግሞ ካለፉት ስህተቶቻችን እራሳችንን በማረም የተሻለ ዉጤት ለማምጣት ጠንክረን በመስራት ላይ እንገኛለን።
ሀትሪክ :- ሻሸመኔ ከተማ ለሊጉ አዲስ እንደመሆኑ ከእሱ ምን እንጠብቅ ? ምን አይነት የዉድድር ዘመን እናሳልፋለን ብለህ ታስባለህ ?
ያሬድ :- ሻሸመኔ ከተማ ለሊጉ አዲስ እንደመሆኑ መጠን ባለፉት ጨዋታዎች ክለባችንን የሚመስል ዉጤት አልያዝንም ነበር በቀጣይ እነዛን ጥቃቅን ስህተቶችን አርመን ጥሩ እና ጠንካራ ተፎካካሪ በመሆን ለሊጉ ድምቀት እንሆናለን ብዬ አስባለሁ።
ሀትሪክ :- በግልህ ስላሳካሀቸዉ ስኬቶችህ አጫዉተን ? እንዲሁም እንደ ቡድን ስላሳካሀቸዉ ስኬቶችም ?
ያሬድ :- በግሌ አሳክቼዋለሁ የምለዉ ትልቁ ታሪካዊ ስኬቴ በወላይታ ዲቻ እያለሁ በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ካፕ ዛማሌክን ስናሸንፍ ያስቆጠርኳት ጎል ስትሆን እንዲሁም እንደ ቡድን ከወላይታ ዲቻ ጋር በኮንፌዴሬሽን ካፕ እስከ ጥሎ ማለፍ ድረስ የሄድነዉ ሲሆን ሲቀጥል ደግሞ ዘንድሮ ከ15 ዓመት በኋላ ሻሸመኔ ከተማ በሊጉ ላይ ሲሳተፍ የክለቡን የመጀመሪያ ጎል ያስቀጠርኩ ታሪካዊ ተጫዋች ሆኛለሁ።
ሀትሪክ :- ስለ ሻሸመኔ ከተማ የአንተ ምልከታ ምንድነዉ ?
ያሬድ :- ሻሸመኔ ከተማ በእኔ ምልከታ ጥሩ ቡድን ነዉ በተለይ በወጣቶች የተገነባ ቡድን ነዉ። ግን ጥቃቅን ስህተቶች ዋጋ አስከፍለዉን ከዚህ በፊት ዉጤት አተናል ያን አስተካክለን ጥሩ ቡድን እንገነባለን።
ሀትሪክ :- ሻሸመኔ ዘንድሮ ምን አይነት ዉጤት ያስመዘግባል ብለህ ታስባለህ ?
ያሬድ :- ሻሸመኔ አሁን ያለበት ደረጃ እና አጨዋወቱ ደጋፊዉን የሚመጥን አይደለም። እሱን በቀጣይ ባሉን ጊዜያት አስተካክለን ደጋፊዉን ለማስደሰት ጠንክረን እየሰራን ነዉ። ስለዚህ ሻሸመኔ ከተማ ጥሩ ደረጃ ይዞ ይጨርሳል ብዬ አስባለሁ።
ሀትሪክ :- በእስከዛሬዉ የእግር ኳስ ህይወትህ የሚያስደስት እና የሚያስከፋ ጊዜን አሳልፌበታለሁ ብለህ የምታስበዉን አጋጣሚ አስታዉሰን ?
ያሬድ :- በእስከዛሬው የእግር ኳስ ህይወቴ የሚያስደስተዉ የነበረዉ ጊዜዬ ወላይታ ዲቻ ዛማሌክን ሲያሸንፍ የማሸነፊያ ጎል በማስቆጠሬ ሲሆን የሚያስከፋዉ ጊዜዬ ደግሞ በእዛዉ አመት ወላይታ ዲቻ ላለመዉረድ ሲጫወት ያሳለፍኩት የጭንቀት ጊዜ ነበር።
ሀትሪክ :- በእግር ኳስ ህይወትህ “ይሄ በሆነ” ወይም “ይሄ ባልሆነ” ብለህ የሚቆጭህ ነገር አለ ?
ያሬድ :- እግዚአብሔር የፈቀደዉ ነገር ብቻ ስለሚሆን ይሄ በሆነ ይሄ ባልሆነ ብዬ አልቆጭም። ምክንያቱም ሁሉም ነገር ሲሆን ለበጎ ነዉ እግዚአብሔር አዋቂ ነዉ።
ሀትሪክ :- ያሬድ እዚህ ለመድረሱ ትልቁን አሻራ ያሳረፈዉ ማነዉ ?
ያሬድ :- ወላጅ እናት እና አባቴ ትልቁን አሻራ ያሳረፉ ሲሆን እንዲሁም በፕሮጀክት እያለሁ የአለኝታ አሰልጣኝ የነበረዉ አብነት ዶኔ እና መሳይ ተፈሪ ትልቁን አሻራ አሳርፈዋል።
ሀትሪክ :- ለእግር ኳስ ህይወቴ አርአያዬ ነዉ የምትለዉ ተጫዋች ማን ነዉ ?
ያሬድ :- ለእግር ኳስ ህይወቴ አርአያዬ ነዉ የምለዉ ተጫዋች ተስፋዬ አለባቸዉ (ቆቦ) ነዉ ምክንያቱም አልሸነፍ ባይነቱ እልሁ ወኔዉ በጣም ደስ ይለኛል።
ሀትሪክ :- ስለ ብሄራዊ ቡድን ምን ታስባለህ ?
ያሬድ :- ኢትዮጵያዊ ተጫዋች ሆነህ የብሄራዊ ቡድን ማለያ ከመልበስ በላይ የሚያስደስት ነገር የለም። እዛ ቦታ ለመድረስ እኔም ጠንክሬ ሰራለሁ። ከፈጣሪ ጋርም ይሳካልኛል።
ሀትሪክ :- ከሀገር ዉስጥ እና ከሀገር ዉጪ የምታደንቃቸዉ ተጫዋቾች እነማን ናቸዉ ?
ያሬድ :- ከሀገር ዉስጥ የሳላዲን ሰይድ አድናቂ ስሆን ከሀገር ዉጪ የሊዮኔል ሜሲ አድናቂ ነኝ።
ሀትሪክ :- ትርፍ ጊዜህን የት ነዉ የምታሳልፈዉ ?
ያሬድ :- ትርፍ ጊዜዬን አብዛኛዉ ጊዜ በመተኛት ነዉ የማሳልፈዉ።
ሀትሪክ :- ስለ ቤተሰብ ሁኔታ አጫዉተን ? ትዳር ፣ ልጆች..?
ያሬድ :- አግብቻለሁ በቅርቡ ደግሞ የወንድ ልጃ አባት ሆኛለሁ። አጋጣሚ እዚህ እያለሁ ነበር ልጄ የተወለደዉ።
ሀትሪክ :- የወደፊት እቅድህ ምንድነዉ ?
ያሬድ :- የወደፊት እቅዴ ጠንክሮ በመስራት ሀገሬን ወክሎ መጫወት ሲሆን ሀገርን ወክሎ በመጫወት የሚመጡ እድሎችንም መጠቀም እፈልጋለሁ።
ሀትሪክ :- ያሬድ ተጫዋች ባይሆን ኖሮ ምን ይሆን ነበር ?
ያሬድ :- አገልጋይ ወይም ሹፌር እሆን ነበር።
ሀትሪክ :- በስተመጨረሻም ማመስገን የምትፈልጋቸዉ አካላት ካሉ እድሉን ልስጥህ ?
ያሬድ :- ከሁሉ በፊት እዚህ ላደረሰኝ ልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋናዬ ይድረሰዉ። በመቀጠል ወላጅ እናት እና አባቴን ማመስገን እፈልጋለሁ እንዲሁም እዚህ እንድደርስ ከልጅነት ጀምሮ በፕሮጀክት ደረጃ ያሰለጠነኝን አሰልጣኝ አብነት ዶኔን ማመስገን እፈልጋለሁ። ከእሱ በመቀጠል ደግም ከወላይታ ዲቻ B ቡድን በማሳደግ እዚህ እንድደርስ የቀረፀኝን አሰልጣኝ መሳይ ተፈሪን ማመስገን እፈልጋለሁ።
እንዲሁም እናንተንም ሀትሪክ ስፖርቶችን እንግዳችሁ አድርጋችሁ ስላቀረባችሁኝ አመሰግናለሁ።
ሀትሪክ :- ስለነበረን ቆይታ እናመሰግናለን።
ያሬድ :- እኔም አመሰግናለሁ።