በሊጉ የመጀመሪያ ሁለት መርግብሮችን ካሸነፉ በኋላ በተከታታይ ሶስት ጨዋታዎች ከድል ጋር ተራርቀው የነበሩት ወልቂጤ ከተማዎች ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፈዋል ።
ወልቂጤ ከተማዎች በአምስተኛው ሳምንት በሲዳማ ቡና በተረቱበት ጨዋታ ከነበረው ምርጥ አስራአንድ ላይ ሶስት ለውጦችን በማድረግ ጀማል ጣሰው ፤ ፍፁም ግርማ እና ጌታነህ ከበደን በሮበርት አዶንካራ ፤ ብርሀኑ ቦጋለ እና ተመስገን በጅሮንድ ተክተው ሲገቡ በኢትዮ ኤሌክትሪክ በኩል በሳምንቱ ከአዳማ ከተማ ነጥብ በተጋሩበት ጨዋታ ላይ የተጠቀሙትን የመጀመሪያ አሰላለፍ ሙሉ ለሙሉ ተጠቅመዋል ።
ፈጠን ባለ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ የጀመረው ጨዋታ ገና ከጅምሩ ግብ ሊያስተናግድ ነበር ።
የጨዋታውን የመጀመሪያ የግብ ሙከራ በሁለተኛው ደቂቃ ለዬ ሲደረግ የኢትዮ ኤሌክትሪሱ ተከላካይ አንዳርጋቸው ይላቅ በአግባቡ ማራቅ ያቃተውን ኳስ ጌታነህ ከበደ አግኝቶ ወደ ግብ ሞክሮ ለጥቂት ኢላማውን ሳይጠብቅ ቀርቷል ።
- ማሰታውቂያ -
ወልቂጤ ከተማዎች የተሻሉ በነበሩበት በዚህ ጨዋታ በጥሩ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ በተደጋጋሚ ወደ ተጋጣሚ አደጋ ክልል ኳሶችን ማድረስ ችለው ነበር ።
በአንፃሩ በኢትዮ ኤሌክትሪክ በኩል ቀደም ብለው ከነበሩት ጨዋታዎች መጠነኛ መቀዛቀዝ ታይቶባቸዋል ።
ወልቂጤ ከተማዎች በፋሲል አበባየሁ አማካይነት በ16ኛው ደቂቃ ላይ ከሳጥን ውጪ ወደ ግብ ያደረጉት ሙከራ ለጥቂት ወደ ውጪ ወጥቷል ።
በ25ኛው ደቂቃ ላይም ጨዋታው የመጀመሪያውን ግብ አስተናግዷል ። ጌታነህ ከበደ ከግራ መስመር የተሻገረለትን ኳስ በግንባር በመግጨት ወልቂጤ ከተማን ቀዳሚ ያደረገ ግብ አስቆጥሯል ።
ወልቂጤ ከተማዎች ከግቡ በኀላም እስከ አጋማሹ መጠናቀቂያ ድረስ ተጭነው መጫወት ችለዋል ።
በጨዋታው 39ኛው ደቂቃ ላይ የኢትዮ ኤሌክትሪኩ ሚክያስ መኮንን ጉዳት አጋጥሞት ጨዋታውን መቀጠል ባለመቻሉ ከሜዳ ለመውጣት ተገዷል ።
የመጀመሪያው አጋማሽም በወልቂጤ ከተማ የ1 ለ 0 መሪነት ተጠናቀቀ ።
የሁለተኛው አጋማሽ በፈጣን የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ ሲጀመር ወልቂጤ ከተማዎች አጋማሹ በተጀመረ ሰባተኛ ደቂቃ ላይ ሌላ ግብ አክለዋል ።
ከሳጥኑ አቅራቢያ በየኋላሸት ላይ በተሰራ ጥፋት የተገኘውን የቅጣት ምት ጌታነህ ከበደ በቀጥታ ወደ ግብ መቶ አስቆጥሮታል ።
ከግቡ በኋላ ኢትዮ ኤሌክትሪኮች ተጭነው ለመጫወት ጥረቶችን አድርገዋል ። ። በተደጋጋሚም በተለይም ከማዕዝን ምቶች ዕድሎችንም ለመፍጠር ችለው ነበር ።
ወልቂጤ ከተማዎች በአንፃሩ ከኳስ ጀርባ በመሆን ጥንቃቄ ላይ ያተኮረ አጨዋወትን የተከተሉ ሲሆን በተወሰኑ አጋጣሚዎች በፈጣን መልሶ ማጥቃት ተጨማሪ ግቦችን ለማግኘት ያደረጓቸው ሂደቶች ውጤታማ ሳይሆኑ ቀርተዋል ።
የአሰልጣኝ ክፍሌ ቦልተናው ቡድን በተለይም በግራ መስመር በኩል በፀጋ ደርቤ አማካኝነት የወልቂጤ ከተማን የኋላ ክፍል ሰብረው ለመግባት ጥረቶችን አድርገዋል ።
ያለ ጠንካራ የግብ ሙከራ እስከ መጨረሻው ደቂቄ በተጓዘው ጨዋታ በ90ኛው ደቂቃ ላይ አቤል ነጋሽ ከአድናን ፈይሰል የደረሰውን አስደናቂ ኳስ ሳይጠቀምበት ቀርቷል ።
የጨዋታው መጠናቀቅ ፊሽካ በሚጠበቅበት ወቀት ኢትዮ ኤሌክትሪኮች የቅጣት ምት ያገኙ ሲሆን በቀጥታ ወደ ግብ የተመታው ኳስ የግቡን አግዳሚ ለትሞ ሲመለስ ያገኘው ታፈሰ ሰርካ በግንባር በመግጨት ከመረብ አሳርፏል ።
በመጨረሻም ወልቂጤ ከተማ ከጨዋታው ሙሉ ሶስት ነጥቦችን ይዞ መውጣት ችሏል ።
በሰባተኛው ሳምንት ጨዋታዎች በመጪው ህዳር 1(ሐሙስ) 10:00 ላይ ወልቂጤ ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን ሲገጥም ህዳር 2(አርብ) በተመሳሳይ ሰዓት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከ ኢትዮጵያ መድኅን ይገጥማል ።