በሀያ ዘጠነኛዉ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የመጨረሻ ዕለት ጨዋታ ቀዳሚ መርሐግብር የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሻሸመኔ ከተማን 2ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
በተመጣጣኝ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ንግድ ባንኮች በተደጋጋሚ ጥሩ ጥሩ የሚባሉ የግብ ዕድሎችን በመፍጠር ረገድ የተሻሉ የነበሩ ቢሆንም ነገር ግን ያገኟቸዉን ዕድሎች ወደ ግብነት በመቀየር ረገድ ግን ደካማ ሁነዉ ተስተውሏል።
በዚህ ሂደት በጀመረዉ ጨዋታ በተቃራኒው ሻሸመኔ ከተማዎች በተደራጀ መከላከል በጨዋታዉ የመጀመሪያው አጋማሽ ሲንቀሳቀሱ የተስተዋለ ቢሆንም ነገር ግን በ40ኛዉ ደቂቃ ላይ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ አግኝተዋል። በዚህም በተጠቀሰዉ ደቂቃ ባሲሩ ዑመር ያሻማትን ኳስ ሱለይማን ሀሚድ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡ አጋማሹን በመሪነት እንዲያጠናቅቅ አስችሏል።
በሁለተኛዉ አጋማሽ ባንኮች የበለጠ ተጠናክረዉ ወደ ሜዳ ሲመለሱ በተቃራኒው ሻሸመኔ ከተማዎች ደግሞ ከመጀመሪያው አጋማሽ በተለየ ተዳክመዉ እና ተቀዛቅዘዉ ሲንቀሳቀሱ የተስተዋለ ሲሆን በሙከራ ረገድም በአንድ ሁለት አጋጣሚ ጥሩ ሙከራ ያደረጉት ባንኮች በ63ተኛዉ ደቂቃ ላይ ተጨማሪ ግብ አግኝተዋል። በዚህም ከግራ መስመር በኩል የተሰጠዉን የቅጣት ምት ኳስ የመስመር አጥቂዉ አዲስ ግደይ በግሩም ብቃት ወደ ግብነት በመቀየር የክለቡን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሪነት ወደ ሁለት ለዜሮ ከፍ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ከግቧ መቆጠር በኋላ የባንኩ የፊት መስመር ተጫዋች ኤፍሬም ታምራት ከወደ ግራ መስመር በኩል በመልሶ ማጥቃት ያገኘዉን ኳስ ተቆጣጥሮ ሳጥን ዉስጥ ደርሶ በቀጥታ ወደ ግብ መትቶ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን በግብ ዘቡ አቤል ማሞ አማካኝነት ኳሷ ተመልሳለች። ሁለቱ ጎሎች ከተቆጠሩ በኋላ ጨዋታዉ ተጋግሎ የቀጠለ ሲሆን በተለይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንኮች በተሻለ በርካታ የግብ ዕድሎችን ማግኘት ቢችሉም ነገር ግን በመጠቀሙ ረገድ ተዳክመዉ ተመልክተናቸዉ ጨዋታዉም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 2ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።
( በተመሳሳይ ሰዓት በሀዋሳ አርቲፊሻል ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ ወልቂጤ ከተማ ሀምበሪቾ ዱራሜን በጋዲሳ መብራቴ ጎሎች ታግዞ 2ለ0 በሆነ ዉጤት በማሸነፍ በሊጉ መቆየታቸዉን ሲያረጋግጡ ፤ በተቃራኒው ሻሸመኔ ከተማ ደግሞ ባደገበት አመት ከሊጉ መዉደቁን አረጋግጧል )
በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ መቻል አዳማ ከተማን 3ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
በፈጣን ሽግግር በጀመረዉ የአመሻሹ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ መቻሎች ገና ከጅምሩ አንስቶ የተሻለ ብልጫ ያስመለከቱን ሲሆን በአምስተኛዉ ደቂቃ ላይም መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም በረከት ደስታ ተከላካዩ ጀሚል ያዕቆብን ተጭኖ በመቀማት ያገኘዉን ኳስ እየገፋ ሄዶ ሳጥን ውስጥ ከገባ በኋላ ተፈጥሯዊ ባልሆነዉ ዕግሩ ኳሷን ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን በጊዜ መሪ ማድረግ ችሏል።
ገና በጊዜ ከተቆጠረችዉ ግብ በኋላ ምላሽ ለመስጠት መጣር የጀመሩት አዳማ ከተማዎች ለግብ የቀረበ ዕድል ማግኘት ችለዉ ነበር ፤ በዚህም ከግራ መስመር በኩል አህመድ ረሽድ ገፍቶ ያቀበለዉን ኳስ አድናን ረሻድ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ኳሷ አላማዋን ሳትጠብቅ ወደ ዉጭ ወጥታለች።
ጥሩ ብልጫ የነበራቸዉ መቻሎች በ20ኛዉ ደቂቃ ላይ አዳማዎች በሰሩት ስህተት የተገኘዉን ኳስ ወደ ግብነት መቀየር ችለዋል ፤ በዚህም በተጠቀሰዉ ደቂቃ ከወደ ግራ በኩል ኳሷን እየገፋ ሳጥን ዉስጥ የገባዉ ሽመልስ በቀለ ለአጥቂዉ ምንይሉ ያቀበለዉን ኳስ ደርሶ ለማቋረጥ የሞከረዉ አህመድ ረሽድ ራሱ መረብ ላይ አሳርፏታል።
ጫናቸዉን ይበልጥኑ አጠናክረዉ የቀጠሉት መቻሎች በተጨማሪም በአማካዩ በሀይሉ አማካኝነት ከሳጥን ዉጭ ከርቀት የሚገርም ሙከራ ማድረግ ችለዉ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ኳሷ ለጥቂት በግቡ አግዳሚ አናት ላይ ወደ ዉጭ ወጥታለች።
በርከት ያሉ ተጫዋቾችን ቀይረዉ ወደ ሜዳ ያስገቡት አዳማ ከተማዎች ያሰቡትን ያክል ጫና መፍጠር ባይችሉም በአድናይ ረሻድ ፣ ቦና አሊ እና ቢኒያም አይተን አማካኝነት ሊጠቀሱ የሚችሉ ሙከራዎችን ማድረግ ችለዉ ነበር ፤ በ77ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግን በጨዋታዉ ድንቅ የነበሩት መቻሎች በአማካዩ ሽመልስ በቀለ ግሩም ብቃት ታግዘዉ ሶስተኛ ግብ አስቆጥረዉ ጨዋታዉ 3ለ0 በሆነ ዉጤት በመቻል አሸናፊነት ተጠናቋል።