ሊጠናቀቅ የሶስት ሳምንታት ዕድሜ ብቻ በቀረዉ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሀያ ስምንተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ዕለት ጨዋታ ፋሲል ከነማ ሻሸመኔ ከተማን ማሸነፍ ችሏል።
በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ቴዎድሮስ ምትኩ ፊሽካ ቀን ዘጠኝ ሰዓት ሲል መከናወን በጀመረዉ የዕለቱ ቀዳሚ ጨዋታ ሻሸመኔ ከተማዎች ገና በጅምሩ በተደጋጋሚ ወደ አፄዎቹ የግብ ክልል መድረስ ሲጀምሩ ካደረጓቸዉ ሙከራዎች መካከልም እዮብ ገ/ማርያም አሻምቷት ሁዛፍ አሊ የሞከራት ኳስ አንዷ ስትሆን ከዚህ በተጨማሪም በ24ተኛዉ ደቂቃ ላይ እንዲሁ በድጋሚ መነሻዉን ከእየብ ያደረገን እጅግ ለግብ የቀረበ ኳስ ሁዛፍ ወደ ግብ ቢሞክርም ነገር ግን ሚካኤል ሳማኬ መልሶበታል።
አሁንም ጫናቸዉን አጠንክረዉ መጫወታቸዉን የቀጠሉት ሻሸመኔዎች በገዛኸኝ ደሳለኝ አማካኝነት ከቅጣት ምት ድንቅ ሙከራ ቢያደርጉም የግቡ አግዳሚ መልሶባቸዋል። በተቃራኒው በአጋማሹ ጨና ለመፍጠር የቸገሩት አፄዎቹ ተጠቃሽ ሙከራ ሳያደርጉ አጋማሹ ተጠናቋል።
በተቀዛቀዘ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ መከናወን በቀጠለዉ ሁለተኛዉ አጋማሽም አሁንም መጠነኛ ብልጫ የተወሰደባቸዉ አፄዎቹ ግን በ76ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ አስቆጥረዉ ጨዋታውን መምራት ጀምረዋል። በዚህም አለምብርሀን ላይ በተሰራ ጥፋት የተሰጠዉን ፍፁም ቅጣት ምት አጥቂዉ ፍቃዱ አለሙ አስቆጥሮ ክለቡን መሪ አድርጓል።
- ማሰታውቂያ -
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታም በ90+2 ላይ ፍቃዱ አለሙ ከናትናኤል ገ/ጊዮርጊስ የተቀበለውን ኳስ ወደ ግብነት ቀይሮ የክለቡን መሪነት ወደ ሁለት ለዜሮ ከፍ ማድረግ ችሎ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን አስገራሚ በነበረዉ የመጨረሻ ደቂቃ ሻሸመኔ ከተማዎች በአጥቂዉ ሁዛፍ አሊ አማካኝነት ግብ አስቆጥረዉ ጨዋታዉ በፋሲል ከነማ 2ለ1 አሸናፊነት ተጠናቋል።
በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ ሀዋሳ ከተማ እና ወልቂጤ ከተማ ሁለት አቻ ተለያይተዋል ።
አመሻሽ አስራ ሁለት ሰዓት ሲል በዋና ዳኛ ኢያሱ ፈንቴ መሪነት በጀመረዉ የዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ በሜዳዉ የመሐል ክፍል አልፎ አልፎ ይታዩ ከነበሩ እንቅስቃሴዎች በስተቀር ያን ያህል ተጠቃሽ ሙከራም ሆነ የሜዳ ላይ እንቅሰቃሴን ሳያስመለክተን ጨዋታዉ ለግማሽ ሰዓት ያክል ዘልቆ ግብ ተቆጥሮበታል። በዚህም በ32ተኛዉ ደቂቃ ላይ የሀዋሳ ከተማዉ ተጫዋች አብዱልባሲጥ ከማል ከርቀት ድንቅ ግብ አስቆጥሮ ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
ከዚች ግብ መቆጠር በዘለለ ይህ ነዉ የሚባል ተጠቃሽ ሙከራን በሁለቱም በኩል ሳያስመለክተን የቀጠለዉ የመጀመሪያው አጋማሽ በሀዋሳ መሪነት ተገባዶ ሁለተኛዉ አጋማሽ ተጀምሯል። በዚህም ሁለተኛዉ አጋማሽ እንደተጀመረ የሀዋሳዉ ተከላካይ በረከት ሳሙኤል ጋዲሳ መብራቴ ላይ በሰራዉ ጥፋት የተሰጠዉን ፍፁም ቅጣት ምት ራሱ ጋዲሳ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን አቻ አርጓል።
በተመሳሳይ ደግሞ በ64ተኛዉ ደቂቃ ላይ የወልቂጤዉ ተጫዋች ወሀብ አዳማስ አሊ ሱለይማን ላይ በሰራዉ ጥፋት የተሰጠዉን ፍፁም ቅጣት ምት ራሱ አሊ ማስቆጠር ችሏል። ከነዚህ ግቦች መቆጠር በኋላ በውዝግብ ታጅቦ በቀጠለዉ የጨዋታዉ ቀሪ ደቂቃዎች በ82ተኛዉ ደቂቃ ላይ ጋዲሳ መብራቴ ከቅጣት ምት አስደናቂ ግብ አስቆጥሮ ክለቡን አቻ ማድረግ ችሎ ጨዋታዉም ሁለት አቻ በሆነ ዉጤት ፍፃሜዉን አግኝቷል። ይህንን ተከትሎም ሰራተኞቹ ከሰባት ሳምንታት በኋላ ነጥብ ማግኘት ችለዋል።