በሊጉ የሶስተኛ ሳምንት ቀዳሚ ጨዋታ አርባምንጭ ከተማ መቻልን በመርታት የውድድር ዓመቱ ቀዳሚ ሶስት ነጥቡን አግኝቷል ።
መቻል በሁለተኛው ሳምንት በአዳማ ከተማ በተረቱበት ጨዋታ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ
ሶስት ለውጦችን ያደረጉ ሲሆን በቶማስ ስምረቱ ፤ በሀይሉ ግርማ እና ተሾመ በላቸው ምትክ አሚን ነስሩ ፤ ተስፋዬ በላቸውን እና ሳሙኤል ሳሊሶን ያሰለፉ ሲሆን በአርባምንጭ ከተማ በኩል ደግሞ በሳምንቱ በኢትዮጵያ መድኅን በአስገራሚ ሁኔታ ከተሸነፉበት ጨዋታ አምሰት ለውጦችን በማድረግ አቤል ማሞ ፤ በርናንድ ኦቼንጌ ፤ ወርቅይታደስ አበበ ፤ አሸናፊ ፊዳ እና አሸናፊ ኤልያስን በማሰለፍ ይስሀቅ ተገኝ፤ እዮብ በቀታ ፤ ሙና በቀለ ፤ ተመስገን ተስፋዬ እና አህመድ ሁሴንን በተጠባባቂ ወንበር ላይ አስቀምጠው ጨዋታውን ጀምረዋል ።
በጨዋታው መቻሎች ኳስን ከኋላ መስርተው በመውጣት ወደ አርባምንጭ ከተማ የግብ ክልል የመድረስ አላማን ይዘው የገቡ ቢመስሉም በተደራጀ የመከላከል አንቅስቃሴ ጨዋታውን ያደረጉት አዞዎቹ ይህን በቀላሉ ከማድረግ አግደዋቸዋል ።
- ማሰታውቂያ -
መቻሎች ምንም እንኳን በተለይም በመሀል የሜዳው ክፍል ላይ እንደፈለጉት ለመንቀሳቀስ የተቸገሩ ቢሆንም በመስመሮች በኩል የአዞዎቹን የኋላ ክፍል ሰብረው ለመግባት ጥረቶችን አድርገዋል ።
በጨዋታው 24ኛው ደቂቃ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ መቻል የግብ ክልል የደረሱት አርባምንጭ ከተማዎች መሪ የሆኑበትን ግብ አስቆጥረዋል ። ቡታቃ ሸመና ባልተጠበቀ ሁኔታ በሳጥን ውሰጥ የላከለትን ኳስ አሸናፊ ኤልያስ ከመረብ አሳርፎታል ።
የአርባ ምንጭ ከተማ መሪነት ከስደስት ደቂቃዎች የዘለቀ አልነበረም ። በ29ኛው ደቂቃ ላይ ከቀኝ መስመር የተሻገረውን ኳስ በርናርድ ኦቼንጌ በእጁ በመንካቱ የተሰጠዉን የፍፁም ቅጣት ምት ምንይሉ ወንደሙ አስቆጥሮታል ።
በ37ኛው ደቂቃ ላይ ሳሙኤል ሳሊሶ ከቅጣት ምት በቀጥታ ወደ ግብ የመታው ኳስ በአቤል ማሞ ተመለሰ እንጂ መቻልን መሪ ሊያደርግ የሚችል ነበር ።
በተለይም ከኳስ ውጪ ጥሩ ጊዜን በማሳለፍ ላይ የነበሩት አርባምንጭ ከተማዎች የመጀመሪያው አጋማሽ ከመጠናቀቁ አንድ ደቂቃ ቀደም ብሎ ሁለተኛ ግብ አስቆጥረዋል ። የመጀመሪያው ግብ ሲቆጠር አመቻችቶ ያቀበለው ቡታቃ ሸመና በግሩም ሁኔታ ወደ ግብ ክልል ያሻገረውን ኳስ ተመስገን ደረሰ በተክለማርያም ሻንቆ መረብ ላይ አሳርፏል ።
በሁለተኛው አጋማሽ መቻሎች ዳግም ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረቶችን ያደረጉ ሲሆን የአርባምንጭ ከተማ ሳጥን ውሰጥ መግባት ግን አዳጋች ሆኖባቸው ነበር ። በዚህም ኳሶችን ከርቀት ለመሞከር የተገደዱ ሲሆን በተስፋዬ አለባቸው ፤ ፍፁም አለሙ እና ከነአን ማርክነህ አማካኝነት ያደረጓቸው የግብ ሙከራዎች ውጤታማ መሆን ሳይችሉ ቀርተዋል ።
በአርባምንጭ ከተማ በኩል ይዘው የገቡትን የጨዋታ እቅድ በተገቢ ሁኔታ መተግበር የቻሉ ሲሆን በተወሰኑ አጋጣሚዎች በመልሶ ማጥቃት ዕድሎችን ለመፍጠር ችለው ነበር ።
በተለይም በ64ኛው ደቂቃ ላይ ተቀይሮ የገባው ሱራፌል ዳንኤል ከግራ መስር አቅጣጫ ያሻገረውን ኳስ ወርቅይታደስ አበበ አግኝቶ ሳይጠቀምበት የቀረው ኳስ ለአዞዎቹ አስቆጪ ነበር ።
በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ላይ በአሰልጣኝ ፋሲል ተካልኝ የሚመሩት መቻሎች ግብ ለማግኘት ያደረጓቸው ጥረቶች ሳይሳኩ ጨዋታው በአርባምንጭ ከተማ የ2 ለ 1 አሸናፊነት ተጠናቋል ።
በአራተኛ ሳምንት ጨዋታዎች በመጪው ጥቅምት 9 (ረቡዕ) 7:00 ላይ አርባምንጭ ከተማ ሀድያ ሆሳዕናን የሚገጥም ሲሆን ጥቅምት 11 (አርብ) በተመሳሳይ ሰዓት መቻል ከፋሲል ከነማ ይጫወታል ።