በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት አራተኛ ቀን ውሎ በቀዳሚነት የተገናኙት አርባምንጭ ከተማ እና ሲዳማ ቡና በአንድ አቻ ውጤት ተለያይተዋል ።
አርባምንጭ ከተማዎች በ10ኛ ሳምንት በወላይታ ድቻ በተሸነፉበት ጨዋታ ከነበረው ቋሚ አሰላለፍ የአምስት ተጫዋቾች ቅያሪ ያደረጉ ሲሆን ይስሀቅ ተገኝ ፣ ወርቅይታደስ አበበ ፣ አሸናፊ ኤልያስ ፣ ሀቢብ ከማል እና ፀጋዬ አበራን በሳምሶን አሰፋ ፣ ሙና በቀለ ፣ ደረጄ ፍሬው ፣ ራምኬል ሎክ እና አብነት ተሾመ ተክተው ገብዋል ። በሲዳማ ቡና በኩል ደግሞ ባህርዳርን ከረቱበት ጨዋታ አንድ ቅያሪ ብቻ በማደረግ ብሩክ ሙሉጌታን በዳዊት ተፈራ ቀይረው አስገብተዋል ።
በመጀመሪያ አጋማሽ ሲዳማ ቡናዎች ከኋላ መስርተው በመውጣት ለመጫወት ያደረጉት ጥረት በአርባምንጭ ከተማ ተጨዋቾች ጫና ምክንያት በቀላሉ ኳሱን ይዘው ለመውጣት የተቸገሩ ሲሆን በዚህም ረጃጀም ኳሶችን ለመጠቀም ተገደዋል ።
- ማሰታውቂያ -
በ1ኛው ደቂቃ ላይ ደግፌ አለሙ ከቀኝ መስመር የመታው ኳስ በአርባምንጩ ግብ ጠባቂ ሳምሶን አሰፋ ከተያዘ በኋላ ይህ ነው ሊባል የሚችል ግብ ጠባቂዎችን የፈተኑ ሙከራ ለደቂቃዎች አልታዩም ነበር ። 38ኛ ደቂቃ ላይ ግን በሲዳማ ቡና በኩል የመጀመሪያው ግብ ተቆጥሯል ። ከሀብታሙ ገዛኸኝ በግሩም ሁኔታ የደረሰውን ኳስ አጥቂው ይገዙ ቦጋለ አጨራረሱን አሳምሮ ክለቡን ቀዳሚ ማድረግ የቻለ ሲሆን በግሉም የውድድር ዓመቱ 7ኛ ግቡን በማስቆጠር የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን ከሚመራው ከቅዱስ ጊዮርጊሱ እስማኤል ኦሮ ኦጎሮ ጋር እኩል መሆን ችሏል ። የመጀመሪያው አጋማሽም በሲዳማ ቡና መሪነት ተጠናቀቀ ።
በአብዛኛው የሁለተኛው አጋማሽ ክፍለ ጊዜ ጨዋታውን በመምራት ላይ የነበሩት ሲዳማ ቡናዎች እንደ መጀመሪያው አጋማሽ ሁሉ ኳሱን ተቆጣጥረው በመጫወት ወደ ፊት የመሄድ ዕድሎችን ቀድሞ ከነበረው በተሻለ መፍጠር የቻሉበት ሲሆን በአርባምንጭ ከተማ በኩል ደግሞ የሚነጠቁ ኳሶችን በፈጣን እንቅስቃሴ ወደ ተጋጣሚ የሜዳ ክፍል ይዞ በመግባት ግብ ለማግኘት ጥረቶችን ተደርገዋል ።
60ኛ ደቂቃ ላይ ሲዳማ ቡናዎች አከታትለው ሁለት ሙከራዎችን ማድረግ ችለው ነበር ። ይገዙ ቦጋለ በረጅም የደረሰውን ኳስ ተቆጣጥሮ ወደ ግብ ያደረገው ሙከራ በግብ ጠባቂው ሳምሶን አሰፋ ሲያዝ ከሰከንዶች በኋላም ሀብታሙ ገዛኸኝ ከሳጥን ውጪ በግራ እግሩ ወደ ግብ የመታውን ኳስ ሳምሶን አሰፋ በድጋሚ ተቆጣጥሮታል ። 67ኛ ደቂቃ ላይ ሀብታሙ ገዛኸኝ በፈጣን እንቅስቃሴ በቀኝ መስመር ወደ ግብ ክልል ይዞት የገባውን ኳስ ወደ ግብ ቢሞክረውም የግቡ ቋሚ መልሶበታል ።
አርባምንጭ ከተማዎች ቀስ በቀስ ቀድሞ ከነበራቸው የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ የተሻሉ መሆን በቻሉባቸው ደቂቃዎች ላይ ግብ ማግኘት ችለዋል ። 70ኛ ደቂቃ ላይ ሀቢብ ከማል ከርቀት ላይ የተገኘውን የቅጣት ምት መረብ ላይ በማሳረፍ አዞዎቹን አቻ አድርጓል ። ሀቢብ ከማል ግቡን ካስቆጠረ 8 ደቂቃዎች በኋላ በመሀሪ መና ላይ በሰራው ጥፋት በሁለተኛ የቢጫ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል ።
በቀሪዎቹ ደቂቃዎች የቁጥር ብልጫ ያገኙት ሲዳማ ቡናዎች ብልጫ ወስደው የተጫወቱ ቢሆንም በሁለቱም በኩል ተጨማሪ ግብ ሳይስተናገድ ጨዋታው ተጠናቋል ።
ውጤቱን ተከትሎ አርባምንጭ ከተማ ነጥቡን 12 ያደረሰ ቢሆንም በደረጃው ላይ ግን ምንም ለውጥ ሳያደርግ 12ኛ ላይ ሲቀመጥ ሲዳማ ቡና በ15 ነጥብ ወደ 7ኛ ደረጃ ከፍ ብሏል ።
በ12ኛ ሳምንት ጨዋታዎች አርባምንጭ ከተማ ድሬዳዋ ከተማን ሲዳማ ቡና ደግሞ ጅማ አባጅፋርን የሚገጥሙ ይሆናል ።