*…ፌዴሬሽኑ ህጋዊ ነው ያላቸውን ተጨዋቾች ዝርዝር
ለሊግ ኩባንያው ልኳል…..
ለገጣፎ ለገዳዲ በሊግ ኩባንያ የተወሰደው ተገቢነት የሌለው ርምጃ ካልተስተካከለ ከዛሬው የ15ኛ ሳምንት ጨዋታ ራሳችንን እናገላለን” ሲል ክለቡ አስታወቀ።
በሊጉ የ14ኛ ሳምንት መርሃግብር ያስፈረማቸውን ተጨዋቾች ከሁለተኛው ዙር በኋላ እንጂ መሠለፍ አይችሉም በሚል በመከልከላቸው በ12 ተጨዋች ብቻ የገቡት ለገጣፎዎች በሲዳማ ቡና 2ለ0 የተሸነፉ ሲሆን ከወራጅ ቀጠና እንዲያወጣቸው በቀጠሩት አሰልጣኝ ዘማሪያም ወ/ጊዮርጊስ ላይ ሌላ ጫና ፈጥሯል።
ሊግ ኮሚቴው የሲዳማ ቡናና የለገጣፍ ለገዳዲ ጨዋታ አስቀድሞ በተነሳው ውዝግብ ዙሪያ አሰልጣኙና ቡድን መሪውን ትላንት ጠዋት ጠርተው ያነጋገሩ ሲሆን ውዝግብ ከሚያስነሱና ልዩነት ከሚፈጥሩ አስተያየቶች እንዲቆጠቡ የሚዲያ ፍጆታ ከማድረግ እንዲቆጠቡ አሳስበው ውይይቱ ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
ሊግ ከባንያው አንደኛ ዙር ሳያልቅ የዝውውር መስኮቱን መክፈቱ የፈጠረውን ክፍተት ከማረም ባለበት ውሳኔው መቀጠሉ ቅሬታ እንደፈጠረባቸው የገለጹት የክለቡ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ገዛኸኝ እንዳለ.. ” ፌዴሬሽኑ መብታችንን እንዲያስከብር ጠይቀናል በሊግ ኩባንያው አካሄድና ውሳኔ ተከፍተናል ውሳኔውን ገምግሞ ማስተካከያ የማያደርግና ያስፈረምናቸውን ተጨዋቾች እንድንጠቀም የማይፈቄድ ከሆነ ከዛሬው የመቻል ጨዋታ ራሳችንን አግልለናል ይህንንም ለሊግ ኩባንያው አሳውቀናል በደሉና ተገቢ ያልሆነው አካሄድ በኛ መቆም አለበት” ሲሉ ቅሬታቸውን ገልጸዋል።
ሊግ ኩባንያው በተዘጋው የዝውውር መስኮት የፈረሙ ተጨዋችችን መጠቀም የሚቻለው ከ16ኛው ሳምንት ጀምሮ ነው በ14ኛ እና በ15ኛ ሳምንት የተጠቀመ ካለ በፎርፌ ይቀጣል” የሚለውን ደብዳቤ ለ16ቱም ክለቦች የጻፈው ለገጣፎዎች ጥያቄ ካነሱና የሊግ ኩባንያው ዋና ስራ አስኪያጅ ከለገጣፎ ስራ አስኪያጅ ጋር በስልክ ከተነጋገሩ ከሰዓታት በኋላ መሆኑ የክለቡን ቅሬታ አጠናክሮታል።
ዛሬ ጠዋት ከክለቡ ምንጭ በተገኘ መረጃ ፌዴሬሽኑ ህጋዊ የሚላቸውና ዛሬም መጫወት የሚችሉ ተጨዋቾችን ዝርዝር ለሊግ ኩባንያና ለክለቡ መላኩ ታውቋል።