በአስራ ዘጠነኛዉ ሳምንት የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሶስተኛ ቀን ጨዋታ የሊጉ መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስ አዳማ ከተማን 2ለ1 በሆነ ዉጤት በማሸነፍ መሪነቱን አጠናክሮ ቀጥሏል።
ባለፈዉ ሳምንት በሊጉ የአስራ ስምንተኛ ሳምንት መርሐግብር በወራጅ ቀጠናዉ ዞን ላይ ከሚገኘዉ ሲዳማ ቡና ጋር ጨዋታውን አንድ አቻ በሆነ ዉጤት ያጠናቀቀዉ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ከሶስት ተከታታይ ድሎች በኋላ ባሳለፍነዉ ሳምንት በሀዋሳ ከተማ ሽንፈት ባስተናገደዉ ባለሜዳዉ አዳማ ከተማ መካከል በተካሄደው ጨዋታ በተለይ የመጀመሪያዎቹ አስራ አምስት ደቂቃዎች ያህል ሁሉቱም ቡድኖች ተመጣጣኝ የሚባል የጨዋታ እንቅስቃሴን ያስመለከቱን ሲሆን የጨዋታው ደቂቃ እየገፋ በመጣ ቁጥር ግን ፈረሰኞቹ ቶሎ ቶሎ ወደ አዳማ ከተማ የግብ ከልል በመድረስ ረገድ የተሻሉ ሁነዉ ተስተውለዋል።
- ማሰታውቂያ -
በተለይ የአሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ ቡድን ቅዱስ ጊዮርጊስ በአቤል ያለዉ እና የፊት መስመር አጥቂ ኢስማኤል ኦሮ አጎሮ አማካኝነት ጥሩ ጥሩ የሚባሉ ለግብ የቀረቡ ሙከራዎችን ሲያደርጉ በተቃራኒው በመጠኑም ቢሆን ብልጫ የተወሰደባቸዉ የሚመስሉት አዳማዎች ደግሞ አልፎ አልፎ በአሜ መሐመድ ፣ ዮሴፍ ታረቀኝ እና ቦና አሊ አማካኝነት የሚገኙ ዕድሎችን ወደ ግብነት ለመቀየር ሲጥሩ ተስተውሏል። በዚህ ሂደት የቀጠለዉ የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታም የመጀመሪያው አጋማሽ ያለ ግብ በአቻ ዉጤት ተጠናቋል።
ከዕረፍት መልስ ወዲያዉኑ በሁለት ደቂቃዎች ልዩነት አዳማ ከተማዎች በዮሴፍ ታረቀኝ አማካኝነት ለግብ የቀረቡ ሙከራዎችን ማድረግ ቢችሉም ግብ ማስቆጠር ግን አልቻሉም ነበር በ51ኛዉ ደቂቃ ላይ ግን ፈረሰኞቹ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ማግኘት ችለዋል። በዚህም የአዳማ ከተማ ተከላካዮች የሰሩትን ስህተት ተጠቅሞ ኢስማኤል ኦሮ አጎሮ ያቀበለዉ ኳስ አቤል ያለዉ የግል ብቃቱን ተጠቅሞ ግብ በማስቆጠር ቡድኑን መሪ ማድረግ ችሏል።
ፈረሰኞቹ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ካስቆጠሩ ከሀያ ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ሁለተኛ ግብ አስቆጥረዋል። በዚህም በ72ተኛዉ ደቂቃ ቢኒያም በላይ ከርቀት አክርሮ ወደ ግብ የላከዉን ኳስ ሰይድ ሀሰን ወደ ዉጭ ሲያወጣዉ የተገኘዉን የማዕዘን ኳስ ቶጓዊው አጥቂ ኢስማኤል ኦሮ አጎሮ በጉልበቱ ወደ ግብነት በመቀየር የፈረሰኞቹን መሪነት ወደ ሁለት ከፍ ማድረግ ችሏል።
ሁለት ግብ ከተቆጠረባቸው በኋላ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረት ሲያደርጉ የነበሩት አዳማዎች በ75ተኛዉ ደቂቃ ላይ ወደ ጨዋታው ሊመልሳቸዉ የሚችላቸውን ጎል በዳንኤል ደምሴ አማካኝነት አስቆጥረዋል። ከዚህ ግብ መቆጠር በኋላ አዳማዎች የአቻነት ግብ ለማግኘት ቢጥሩም ውጥናቸዉ ሳይሰምር በቅዱስ ጊዮርጊስ 2ለ1 በሆነ ዉጤት ለመሸነፍ ተገደዋል። ዉጤቱን ተከትሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ42 ነጥቦች መሪነቱን አጠናክሮ ሲቀጥል በተቃራኒው በዕለቱ ሽንፈት ያስተናገደዉ አዳማ ከተማ ደግሞ በ24 ነጥቦች 9ነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።