በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት ጨዋታ የሁለተኛ ቀን የምሽት ጨዋታ ባሳለፍነዉ ሳምንት በሊጉ መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሽንፈት አስተናግዶ የነበረዉ ፋሲል ከነማ የአሰልጣኝ ዘርዓይ ሙሉን ሀዋሳ ከተማ 1ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
በአመዛኙ በአፄዎቹ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ገና ጨዋታዉ በጀመረዉ በ1ኛዉ ደቂቃ ላይም ሀይቆቹ ሀዋሳ ከተማዎች ድንቅ የሚባል ግብ የማግባት ዕድል መፍጠር ችለዋል። በዚህም አብዱልባሲጥ ከቀኝ የሀዋሳ ከተማ ማጥቃት በኩል ያቀበለዉን ኳስ አሊ ሱለይማን ወደ ግብ የሞከራት ኳስ በጨዋታዉ መጀመሪያ ላይ የተደረገች ሙከራ ነበረች።
- ማሰታውቂያ -
ከዚች የመጀመሪያ ደቂቃ ሙከራ በኋላ ደግሞ በ4ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ ጠባቂዉ መሀመድ ሙንታሪ ለአሊ ሱለይማን በቀጥታ ያሻገረለትን ኳስ አሊ እንደምንም ተቆጣጥሮ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ ኢላማዋን ሳትጠብቅ ወደ ዉጭ ወጥታለች።
በጨዋታዉ የመጀመሪያ ደቀቃዎች ላይ በሀዋሳ ከተማዎች ተደጋጋሚ ሙከራ የተደረገባቸዉ ፋሲል ከነማዎችም የመጀመሪያ ሙከራቸዉን በ14ተኛዉ ደቂቃ ላይ ማድረግ ችለዋል። በዚህም አምሳሉ ጥላሁን ያሻማዉን ቅጣት ምት ኳስ አስቻለዉ ታመነ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ለጥቂት ግብ ጠባቂዉ ሙንታሪ ተቆጣጥሯታል።
ከዚች ሙከራ በኋላ ወደ ጨዋታዉ የተመለሱ የሚመስሉት አፄዎቹ በድጋሚ በ25ተኛዉ ደቂቃ በኦሴ ማውሊ አማካኝነት እጅግ ለግብ የቀረበ ድንቅ ሙከራ ማድረግ ችለዉ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ሙንታሪ በድጋሚ ኳሷን ግብ ከመሆን ታድጓታል።
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ላይም በአጋማሹ መጠናቀቂያ ደቂቃ ላይ ኦሴ ማዉሊ በረጅሙ ከመናፍ አወል የተሻገረለትን ኳስ ወደ ግብ በቀጥታ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ ለጥቂት ወደ ዉጭ ወጥታለች።
ከዕረፍት መልስ የነበራቸዉን ብልጫ ያስቀጠሉት አፄዎቹ በ58ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም በዛብህ መለዮ ከግራ በኩል ያሻማዉን ኳስ ግብ ጠባቂዉ መሐመድ ሙንታሪ በቅጡ መቆጣጠር ባለመቻሉ ምክንያት ወደ ግብነት ተቀይራ አፄዎቹ ጨዋታዉን መምራት ጀምረዋል።
መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ካስቆጠሩ በኋላም የማጥቃት ሀይላቸዉን አጠናክረዉ የቀጠሉት አፄዎቹ በናትናኤል ገ/ጊዮርጊስ እና ኦሴ ማዉሊ አማካኝነት ጥሩ የሚባሉ ለግብ የቀረቡ ሙከራዎችን ማድረግ ችለዋል። በተቃራነዉ ግብ ከተቆጠረባቸዉ በኋላ ደግሞ የአቻነት ግብ ፍለጋ የቀጠሉት ሀይቆቹ በ67ተኛዉ ደቂቃ ላይ በአሊ ሱለይማን አማካኝነት ድንቅ የሚባል ለግብ የቀረበን ሙከራ ማድረግ ቢችሉም በግብ ጠባቂዉ ሳማኪ አማካኝነት ከሽፎባቸዋል።
በዚህ ሂደት የቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም ተጨማሪ ግብ ሳይስተናገድበት በአፄዎቹ አንድ ለዜሮ አሸናፊነት ተጠናቋል። ዉጤቱን ተከትሎም ፋሲል ከነማ በ30 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ በተቃራኒው ሀዋሳ ከተማ በ31 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።