በሶስተኛው ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለተኛ ጨዋታ አዳማ ከተማ በዳዋ ሆጤሳ ብቸኛ ግብ ሀዋሳ ከተማን ረቷል ።
በሀዋሳ ከተማ በኩል በሁለተኛው ሳምንት ኢትዮጵያ ቡናን በረቱበት ጨዋታ ላይ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ የሶስት ተጫዋቾች ለውጥ በማድረግ በሰለሞን ወዴሳ ፤ እዮብ አለማየሁ እና አዲሱ አቱላ
ምትክ ላውረንስ ላርቴ ፤ ብርሀኑ አሻሞ እና ኤፍሬም አሻሞን ሲያሰለፉ በአዳማ ከተማ በኩል በሳምንቱ መቻልን በረቱበት ጨዋታ ላይ በነበረው ምርጥ አስራአንድ ላይ ምንም ለውጥ ሳያደርጉ ጨዋታውን ጀምረዋል ።
- ማሰታውቂያ -
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ አዳማ ከተማዎች በተሻለ ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል መድረስ የቻሉ ሲሆን የጠሩ የግብ ዕድሎችን ከመፍጠር አኳያ ግን ክፍተቶች ነበሩባቸው ። በአንፃሩ ሀዋሳ ከተማዎች ከራሳቸው የሜዳ ክፍል ለመውጣት እጅጉን ተቸግረው አብዛኛውን የአጋማሹን ክፍለ ጊዜ በመከላከል እንቅስቃሴ ላይ አሳልፈዋል ።
ለበርካታ ደቂቃዎች ያለ ግብ ሙከራ በመካሄድ ላይ የነበረው ፍልሚያ በ35ኛው ደቂቃ ላይ የመጀመሪያው የግብ ሙከራ ተስተናግዶበታል ።
ኤርትራዊው አሊ ሱሌማን ከመሀል የተላከለትን ኳስ ከሳጥኑ ጠርዝ ግራ አቅጣጫ ወደ ግብ አክርሮ የመታውን ኳስ ግብ ጠባቂው ኩዋሜ ባህ ግብ ከመሆን አድኖታል ።
በ42ኛው ደቂቃ አዳማ ከተማዎች ጥሩ የግብ ዕድል መፍጠር ችለው የነበረ ሲሆን ደስታ ዮሀንስ ከቀኝ መስመር ያሻገረውን ኳስ አብዲሳ ጀማል በግንባር ገጭቶ የግቡ ቋሚ መልሶበታል ።
የመጀመሪያው አጋማሽም ያለ ግብ ተጠናቋል ።
በተመሳሳይ እንቅስቃሴ በቀጠለው የ ሁለተኛው አጋማሽ ሀይቆቹ በቀዳሚው አጋማሽ ከነበራቸው በተሻለ ለመንቀሳቀስ በመሞከር በተለይም ሙጂብ ቃሲምን ኢላማ ያደረጉ ኳሶችን ወደ ተጋጣሚያቸውን የግብ ክልል ለማድረስ ጥረዋል ።
ከሁለተኛው አጋማሽ መጀመር 15 ደቂቃዎች በኋላ አዳማ ከተማዎች ካልታሰበ ቦታ ግብ አግኝተዋል ።
የቡድኑ አምበል ዳዋ ሆጤሳ ከርቀት ወደ ግብ የመታው ኳስ በመድኅኔ ብርሀኔ ተጨርፎ የግብ ጠባቂው አላዛር ሽመልስ ቦታ አያያዝም ታክሎበት ግቡ ሊቆጠር ችሏል ።
ከሁለት ደቂቃዎች በኋላ በሀዋሳ ከተማ በኩል ብርሀኑ አሻሞ ከቆመ ኳስ ያሻገረውን ኳስ አብዱልባሲጥ ከማል በግንባር ገጭቶ ለማስቆጠር ያደረገው ጥረት ለጥቂት ሳይሳካ ቀርቷል ።
በ70ኛው ደቂቃ ላይ ኤፍሬም አሻሞ ከግቡ ትይዪ የተገኘውን የቅጣት ምት አክርሮ ወደ ግብ መሞከር ቢችልም ኳሱ ኢላማውን መጠበቅ ሳይችል ቀርቷል ።
በጨዋታው የመጨረሻ ደቂቃዎች ላይ ሀዋሳ ከተማዎች ቅያሪዎችን በማድረግ የአቻነቱን ግብ ፍለጋ ለማግኘት ቢኳትኑም የአዳማ የኋላ መስመር ይህን የሚፈቅድ አልነበረም ።
በ78ኛው ደቂቃ ላይ ተከላካዩ ሚሊዮን ሰለሞን የአላዛርን አቋቋም ተመልክቶ ወደ ግብ የመታው ኳስ ለጥቂት ወደ ውጪ ወቷል ።
ጨዋታው ሊጠናቀቅ የሰከንዶች ዕድሜ በቀሩት ጊዜ አዳማ ከተማዎች በመልሶ ማጥቃት ጥሩ ዕድል መፍጠር ቢችሉም ዳንኤል ደምሴ አጋጣሚውን ሳይጠቀምበት ቀርቷል ።
በመጨረሻም አዳማ ከተማ በዳዋ ሁጤሳ ብቸኛ ግብ 1 ለ 0 አሸንፏል ።
በአራተኛው ሳምንት ጨዋታዎች በመጪው ጥቅምት 8(ማክሰኞ) አዳማ ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን 7:00 ላይ ሲገጥም 10:00 ላይ ደግሞ ሀዋሳ ከተማ ከወልቂጤ ከተማ ይጫወታል ።