በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የሰላሳኛ ሳምንት ጨዋታ ባህርዳር ከተማ ወላይታ ዲቻን 1ለ0 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
ምንም እንኳን በዉጤት ደረጃ ለሁለቱም ቡድኖች ያን ያህል እንገብጋቢ ባይሆንም በርከት ያሉ የተጫዋቾች ለዉጥ አድርገዉ ወደ ሜዳ በገቡት በሁለቱ ክለቦች የዕለቱ ጨዋታም ተመጣጣኝ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ የተስተዋለ ሲሆን ፤ በመጀመሪያዎቹ ደቂቃዎች ላይ ግን የጣና ሞገዶቹ በሙከራ ረገድ ተሽለዉ ታይተዋል።
በዚህም በመስመር በኩል ጥሩ ሲንቀሳቀሱ የነበሩት የጣና ሞገዶቹ ከቀኝ ተከላካዩ ሳላምላክ ተገኝ የተሻማዉን ኳስ የመስመር አጥቂዉ አደም አባስ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም የግቡ ዘቡ ቢኒያም እንደምንም ኳሷን መልሷታል። ከዚች ሙከራ በተጨማሪም የመሐል ሜዳዉ ተጫዋች ፍ/ሚካኤል አለሙ ከቆመ ኳስ ያብስራ ያሻማዉን ኳስ በግንባሩ በመግጨት ግብ ለማስቆጠር ተቃርቦ ነበር ።
- ማሰታውቂያ -
በተመሳሳይ አይነት የጨዋታ መንገድ ምንም እንኳን በሙከራ ረገድ በተወሰነ መልኩ ብልጫ ይወሰድባቸዉ እንጅ ተመጣጣኝ ፍክክሩ ያደርጉ የነበሩት ዲቻዎች በመጀመሪያዉ አጋማሽ በረጅሙ አጥቂ ስንታየሁ እና በአማካዮቻቸዉ አበባየሁ እንዲሁም መሳይ አማካኝነት ለግብ የቀረቡ ሙከራዎችን ማድረግ ቢችሉም አጋማሹ ለገባደድ አራት ያህል ደቂቃዎች ሲቀሩ ግን ግብ አስተናግደዋል። በዚህም በ41ኛዉ ደቂቃ ላይ አማካዩ ያብስራ ከመዓዘን ያሻገረለትን ኳስ አደም አባስ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
ከዕረፍት መልስ በነበራቸዉ የጨዋታ እንቅስቃሴ ተቀዛቅዘዉ የተመለሱት ሁለቱም ክለቦች ግብ ለማስቆጠርም ሆነ ተጠቃሽ ሙከራዎችን ለማድረግ ተቸግረዉ የተስተዋለ ሲሆን በተለይ የጣና ሞገዶቹ ዲቻዎች የጨዋታዉ ደቂቃ እየገፋ በሄደ ቁጥር ተዳክመዉ እና ተቀዛቅዘዉ ተስተዉለዋል።
በተመሳሳይ ባህርዳር ከተማዎችም በመጀመሪያው አጋማሽ የነበራቸዉን ብልጫ ማስቀጠል ተስኗቸዉ ሲቀጥሉ በርከት ያሉ ተጫዋቾችንም ቀይረዉ ወደ ሜዳ በማስገባት ለመጫዎት ሲጥሩ ቆይተዉ በጨዋታውም ተጨማሪ ግብ ሳይስተናገድ ባህርዳር ከተማ 1ለ0 በሆነ ዉጤት አሸንፏል። ዉጤቱን ተከትሎም የጣና ሞገዶቹ አመቱን በ60 ነጥብ በሁለተኝነት ሲያገባድዱ በተቃራኒው ዲቻዎች ደግሞ በ37 ነጥብ አስራ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ አመቱን ደምድመዋል።