ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ1ኛ ሳምንት የዲሲፕሊን ውሳኔዎች !!
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድርና አመራር ስነስርዓት ኮሚቴ በአንደኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ግጥሚያዎችን በተመለከተ ከዳኞች እና ከታዛቢዎች የቀረቡለትን የዲሲፕሊን ሪፖርት ከመረመረ በኋላ የተለያዩ የዲሲፕሊን ውሳኔዎችን አሳልፏል።
#በተጫዋቾች_ደረጃ:- የድሬዳዋ ከተማዉ ኤልያስ አህመድ ዳኛን አፀያፊ ስድብ በመሳድብ ከጨዋታ ሜዳ የተወገደ ስለመሆኑ ሪፖርት የቀረበበት ሲሆን ለፈፀመው ጥፋት 3 ጨዋታ እንዲታገድና በተጨማሪ የገንዘብ ቅጣት ሶስት ሺ ብር እንዲከፍል እንዲሁም ጊት ጋትኩት ፣ ሽመክት ጉግሳ ፣ ዊሊያም ሰለሞን ሁለተኛ ቢጫ ካርድ የሚያስጥ ጥፋት በመፈፀም ቀይ ካርድ አይተው ከጨዋታ ሜዳ የተወገዱ ሲሆን በዚህም 1 ጨዋታ እንዲታገዱ ተወስኗል።
የድሬዳዋዉ እንየው ካሳሁን ሃይማኖታዊ መልእክት የሚያስተላልፍ ምስል በውስጥ ልብሱ ደርቦ ስለመልበሱ ሪፖርት የተደረገበት በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የውድድር ደንብ መሰረት ተጫዋቹ ሶስት ሺ ብር እንዲከፍል ሲቀጣ እንዲሁም ክለቡ ድሬዳዋ ከተማ ደግሞ አስር ሺህ ብር እንዲከፍል ተወስኗል።
- ማሰታውቂያ -
#በክለብ_ደረጃ :- ድሬደዋ ከተማ በሳምንቱ ጨዋታ የክለቡ አምስት ተጫዋቾች ካርድ የተሰጣቸው በመሆኑ በመመሪያዉ መሰረት አምስት ሺ እንዲከፍል ፣ ኢትዮጵያ መድን ባደረገው ጨዋታ ከዕረፍት መልስ የክለቡ ተጫዋቾች 4 ደቂቃ ወደሜዳ ዘግይተው በመግባሃቸዉ አስራ አምስት ሺህ ብር እንዲከፍል እንዲሁም በዚህ ምክኒያት የቀጥታ ቴሌቭዥን ስርጭት መብት የገዛው ድርጅት የአክሲዮን ማህበሩን የካሳ ክፍያ ከጠየቀ የተጠየቀውን ክፍያ እንዲከፍል ተወስኖባቸዋል።
በተጨማሪም ወልቂጤ ከተማ ባደረገው የሳምንቱ ጨዋታ የክለቡ ተጫዋች ሳሙኤል አስፈሪ ከተፈቀደው የመለያ ቁጥር/1-50/ ውጪ 66 ቁጥር ለብሶ ስለመጫወቱ ሪፖርት የተደረገበት በመሆኑ በደንቡ መሰረት ክለቡ የገንዘብ ቅጣት ሶስት ሺህ ብር እንዲከፍል ተወስኗል፡፡