በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት መርሐግብር የመጀመሪያ ቀን ጨዋታ ባህርዳር ከተማ እና ወልቂጤ ከተማ ቀን 7 ሰዓት ሲል ጨዋታቸዉን አድርገው ወልቂጤ ከተማ ባለ ድል ሆኗል።
የጣና ሞገዶቹ ኢትዮ ኤሌክትሪክን ካሸነፉበት ጨዋታ ፋሲል ገ/ሚካኤልን ፣ መሳይ አገኘሁን ፣ ፍቅረ ሚካኤል አለሙን እና ሀብታሙ ታደሰን በቴፔ አልዛየር ፣ ሰላምላክ ተገኝ ፣ አለልኝ አዘነ እና ቀይረዉ ወደ ሜዳ ሲገቡ በተመሳሳይ ወልቂጤ ከተማዎች ደግሞ ጀማል ጣሰዉን እና ፋሲል አበባየሁን በፋሪስ አላዊ እና ብዙአየሁ ሰይፈ ቀይረዉ ወደ ሜዳ ገብተዋል።
በጨዋታው በአመዛኙ ብልጫ የነበራቸዉ ባህርዳር ከተማዎች የፊት መስመር ተጫዋቾቹን ትኩረትን ያደረጉ ኳሶች በተደጋጋሚ ሲጣሉ የነበረ ቢሆንም ወልቂጤ ከተማዎች በተደራጀ መልኩ በመጫወት የተቃራኒ ቡድንን የማጥቃት እንቅስቃሴ ከማቋረጥ በዘለለ አልፎ አልፎ በሚገኙ ኳሶች በመልሶ ማጥቃት ወደ ባህርዳር የሜዳ ክፍል ሲገቡ ተስተውሏል።
- ማሰታውቂያ -
የጨዋታዉን የመጀመሪያ ሙከራ ለመመልከት ሀያ አምስት ያህል ደቂቃዎች በፈጁበት በአጋማሹ የመስመር ተጫዋቹ ዱሬሳ ሹቤሳ በ25ኛዉ ደቂቃ ላይ ድንቅ ሙከራን ማድረግ ችሏል። በዚህም ከመስመር ተጫዋቹ ሰላምላክ ተገኝ የተሻገረለትን ኳስ ዱሬሳ ከተቆጣጠረ በኋላ ወደ ግብ ሲሞክር ግብ ጠባቂዉ ጀማል ሲመልስ በቅርቡ ይገኝ የነበረዉ ተከላካዩ ዉሀብ አዳምስ በዕጁ ኳሷን ቢመልስም የዕለቱ ዳኛ ባለመመልከታቸዉ ጨዋታዉ እንዲቀጥል ተደርጓል።
በሙከራ ረገድ ደካማ በነበረዉ የመጀመሪያው አጊማሽ ከተመስገን በጅሮንድ የተቀበለውን ኳስ አጥቂዉ ጌታነህ ከበደ ቢሞክርም ኢላማዉን ሳይጠብቅ የቀረዉ ኳስ በክትፎዎቹ በኩል ብቸኛ ሙከራ ነበር።
ከዕረፍት መልስ በቶሎ ወደ ጨዋታ መመለስ የቻሉት ባህርዳር ከተማዎች በ46ኛዉ ደቂቃ ላይ በአማካዩ አለልኝ አዘነ ድንቅ ሙከራን ማድረግ ችለዉ ነበር በዚሁ ደቂቃም ከቀኝ መስመር በኩል ተጨራርፎ የመጣዉን ኳስ አለልኝ አዘነ ከሳጥን ዉጭ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ለጥቂት ወደ ዉጭ ወጥቶበታል። በድጋሚ በ48ኛዉ ደቂቃ ላይ የጣና ሞገዶቹ ድንቅ ለግብ የቀረበ ሙከራን ማድረግ ችለዋል። በዚሁ ደቂቃ ላይም የመስመር ተከላካዩ ሰላምላክ ተገኝ ከቀኝ መስመር በኩል ያሻገረዉን ኳስ ዱሬሳ ሹቤሳ ቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ጀማል ጣሰዉ እንደምንም አዉጥቶታል።
የባህርዳር ከተማዎችን ማጥቃት ሀይል ተቋቁመዉ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረት ሲያደርጉ የነበሩት ወልቂጤ ከተማዎች ዉጥናቸዉ ሰምሮ በ60ኛዉ ደቂቃ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህ ደቂቃ ላይም በዕለቱ ድንቅ የነበረዉ ተመስገን በጅሮንድ ከሳጥን ዉጭ አክርሮ ወደ ግብ የላካት ኳስ የጣና ሞገዶቹ መረብ ላይ አርፋለች።
ከግቧ መቆጠር በኋላ የጣና ሞገዶቹ የማጥቃት ሀይላቸዉን አጠናክረው አቻ ለመሆን ሲጥሩ የነበረ ሲሆን በተቃራኒው እንደ ቡድን ድንቅ የነበሩት ክትፎዎቹ መሪነታቸውን ወደ ሁለት ከፍ ማድረግ የሚችሉባቸዉ አጋጣሚዎች አግኝተዉ የነበረ ቢሆንም ሳይጠቀሙባቸዉ ቀርተዋል። በዚህም በ64ኛዉ ደቂቃ ላይ የመስመር ተጫዋቹ ብዙአየሁ ሰይፈ በረዥሙ ያሻገረለትን ኳስ አጥቂዉ ጌታነህ ከበደ ቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ ለጥቂት ወጥታበታለች። በተቃራኒው በ65ኛዉ ደቂቃ ላይ በባህርዳር ከተማዎች በኩል አደም አባስ ከሳጥን ዉጭ ድንቅ ሙከራ ማድረግ ችሎ የነበረ ቢሆንም በግብ ዘቡ ጀማል ጣሰዉ ጥረት ኳሷ ወጥታለች።
የጨዋታው ሰዓት እየገፋ በመጣ ቁጥር ወልቂጤዎች በይበልጥ ከማጥቃት ይልቅ ዉጤት ወደ ማስጠበቅ ሲያዘነብሉ በተቃራኒው ባህርዳር ከተማዎች የአቻነቷን ግብ ለማግኘት በተደጋጋሚ ኑከራዎችን ማድረግ ቢችሉም ዉጥናቸዉ ሰምሮ ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ በጨዋታዉ ለመሸነፍ ተገደዋል።
በቀጣይ ባህርዳር ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ ጋር የሚገናኙ ሲሆን ወልቂጤ ከተማ ደግሞ ከኢትዮጵያ ቡና ጋር የሶስተኛ ሳምንት ጨዋታቸዉን የሚያደርጉ ይሆናል።