*** “የምትፈልጉት እግርኳሳዊ ለውጥ እንዲመጣ
ከፌዴሬሽኑ ጎን መሆን አማራጭ የለውም”
*** “አንድም ቀን ከሰን አናውቅም….. ተከሰን ግን
አልተሸነፍንም”?
*** “በጀት አልባ ፌዴሬሽን እኛ ነን.. እንደ እግዚአብሄር
ቃል ለፍተን ጥረን ግረን እየሰራን ነው”
*** ” እኛ ዕድሜ እናጭበርብር እናንተ አጋልጡ ከምትሉ እኛ ንጹህ ሆነን የእናንተን ጫና እናቅል ማለት አለባችሁ”
አቶ ደረጄ አረጋ
/የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት/
- ማሰታውቂያ -
“በሶሻል ሚዲያ ያልተጨበጠ ወሬ እየተወራ ባለቀ ሰአት ወደ 2 ሚሊዮን ብር የስፖንሰርሺፕ ገቢ አጥተናል”
ጽ/ቤቱ
“ለክለቦች ድጋፍ ተብሎ የሚበጀት በጀት የለም ወደፊትም አይኖርም…. ክለቦች በራሳቸው የሚቆሙበትን መንገድ መፈለግ እንጂ ድጎማን እንደዋና ባያደርጉት እመክራለሁ”
አቶ አያሌው ታደለ
/የወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ማህበራት
ማደራጃ መምሪያ ዳይሬክተር/
“ጠቅላላ ጉባኤያችሁ ከአጀንዳ ውጪ አይሁን ከመጣችሁበት ጉዳይ ውጪ አትውጡ”
አቶ ባህሩ ጥላሁን
/ የኢት.እግርኳስ ፌዴ.ዋና የስራ አስፈጻሚ/
“ማስ ስፖርትን የሚደግፈው ካናዳ ነው እንዴ..?
መንግስትም እግርኳሱን የግድ መደጎም አለበት..”
ከተሳታፊ
“ዋናው ትጥቅ አምራች ኩባንያ በውል ስምምነታችን መሰረት የሚጠበቅበትን ክፍያ ባለመፈጸሙ ጉዳዩን ወደ ህግ ወስደነዋል” ሲል የአዲስ አበባ ከተማ እግርኳስ ፌዴሬሽን አስታወቀ።
አዲሱ ገበያ አካባቢ በሚገኘው በስቴይ ኢዚ ሆቴል ዛሬ በተካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ተገኝተው ድምጽ ከሚሰጡ 73 አባለት መሃል /56….ክለቦች 9.. ክፍለ ከተማ ፣6.. አመራር ፣ 2….ማህበራት/ 46ቱ በመገኘታቸውና ምልዓተ ጉባኤው በመሟላቱ ጉባኤው ተካሂዷል። ፕሬዝዳንቱ አቶ ደረጄ አረጋ በጉባኤው ላይ እንደተናገሩት “የአዲስ አበባ ከተማ እግርኳስ ዝቅ ብሏል አላደገም የበፊት ታሪካችን ይሄ አይደለም በማለት ስትናገሩ ነበር … በኛ በኩል የምትፈልጉት ለውጥ እንዲመጣ ከፌዴሬሽኑ ጎን መሆን አማራጭ የለውም ጉባኤው በዚህ መንፈስ እንዲካሄድ ጥሪ አደርጋለሁ” በማለት ባደረጉት ንግግር የተጀመረው ጉባኤው የአመታዊ የስራ ሪፖርትም የቀረበ ሲሆን የ11 ክፍለ ከተማ ሜዳዎችን በመጠቀም 134 ክለቦች ውድድራቸውን አካሂደዋል። ፌዴሬሽኑም ከኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ጋር መልካም ግንኙነት የፈጠረበት በርካታ የበጎ ስራ የተሰራበት አመት ሆኗል ተብሏል።
በዚህ ጉባኤ ላይ ትኩረት የተቸረው የፌዴሬሽኑና የዋናው ሀገር በቀል ትጥቅ አምራች ኩባንያ ውል ዙሪያ ከጉባኤው ለተነሳው ጥያቄ በተሰጠው ምላሽ ” ከዋናው ጋር የ3.4 ሚሊዮን ብር ውል ተፈራርመን የነበረ ቢሆንም አንድም ብር አልተቀበልንም ጉዳዩም ወደ ፍርድ ቤት ሄዷል ውጤቱን በቀጣይ የምናየው ይሆናል…የሚል ምላሽ ተሰጥቷል። ፌዴሬሽኑን በተመለከተ ሁለት የቢሮ ሰራተኞች እና ሲሳይ አድርሴ ፕሮሞሽን ጋር የገጠመን ክስ ነው በሁለቱ ክስ አሸንፈናል በሲሳይ አድርሴ ፕሮሞሽን ክስ ሙሉ ወጪ እንዲመልስ ተወስኗል።
በክሱም ረተናል እንደ አዲስ አበባ እግርኳስ ፌዴሬሽን አንድም ቀን ከሰን አናውቅም ተከሰን ግን አልተሸነፍንም” ያሉት አቶ ደረጄ እኛ ገንዘብ ተቸግረናል ለአንድ ኢቨንት ኦርጋናይዘር ግን አንድ ሚሊዮን ብር ይከፈላል ጽ/ቤቱ ከ250 ሺህ ብር በላይ ወጪ ማውጣት አይችልም ለሚለው ጥያቄ ሲመልሱ” እንደ ፌዴሬሽን በጀት ለተያዘላቸው ጉዳዮች ከ250 ሺህ ብር በላይ ማውጣት አይችልም ነገር ግን ዕቅድ ላልተያዘለት ጉዳይ ከ1 ሚሊዮን ብር በላይም ወጪ ማውጣት እንችላለን ለምነን ደጋጎችን ጠይቀን ስፖንሰሮችን አስቸግረን ላገኘነው ብር ገደብ የለውም መጀመሪያ ህጉን እንወቅ” በማለት መልሰዋል።
ስለ ሸገር ሰመርካፕ በተሰጠው ምላሽ ” ከሸገር ሰመር ካፕ አዘጋጆች ጋር ልዩነት ተፈጥሮ ነበር በእኛ በኩል ማንም እየተነሳ የከተማውንም እግርኳስ ልምራ ካለ ዋጋ የምትከፍሉት እናንተ ክለቦች ናችሁ ሸገር ሰመር ካፕ በከተማችን ውድድር ማድረግ የሚችለው የአዲስ አበባ እግርኳስ ፌዴሬሽን መሆኑን አምኖ ውድድሩ ተካሂዷል” ሲሉ ተናግረዋል። ፌዴሬሽኑ ሁለት ቦታ አካውንት ከፍቷል ልክ አይደለም የተባሉት አቶ ደረጄ ” ፌዴሬሽኑ ሁለት ቦታ አካውንት የለውም ውሸት ነው በዳሽን ባንክ ውስጥ አስቀድመው የተከፈቱት ሁለት አካውንቶች እንዲዘጉ አድርገናል ነገር ግን አካውንት መኖሩ ስህተትም አይደለም በጀት አልባ ፌዴሬሽን እኛ ነን እንደ እግዚአብሄር ቃል ለፍተን ጥረን ግረን እየሰራን ነው” በማለት ተናግረዋል።
ስለ እድሜ ማጭበርበር የተጠየቁት አቶ ደረጄ ” ከእድሜ አንጻር እኛ እናጭበርብር እናንተ አጋልጡ ከምትሉ እኛ ንጹህ ሆነን የእናንተን ጫና እናቅል ማለት አለባችሁ ሁለት ቦታ የኤም .አር. አይ ምርመራ መደረጉ የፈጠረውን ጫና ተረድተን አንድ ቦታ ለማድረግ ተስማምተናል” ያሉ ሲሆን ክፍያቸውን በጊዜ ስላላገኙት ኮሚሽነሮችና ዳኞች በሰጡት ምላሽ ” ሁሌም ደጋግመን እንደምንለው ኮሚሽነሮችና ዳኞች እንዲጉላሉ የሞራል ልእልና የለንም ነገር ግን በጊዜው መክፈል አልቻልንም ለተፈጠረው መዘግየት ይቅርታ እንጠይቃለን …. በእግርኳሱ ማንም ሊጉላላ አይገባም ወደ ፊትም አይደገምም” ብለው ቃል ገብተዋል።
“የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫን አልመሰረትንም ግን ለማስቀጠል ታግለናል ከዚህ በኋላ ከከተማችን አይወጣም ወጥቶ የነበረውን ውድድርም መልሰናል
በቀጣይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ሆነን ውድድሩን የምስራቅ አፍሪካ ትልቁ ውድድር ለማድረግ እንጥራለን” ያሉት አቶ ደረጄ ከክለቦች አቅም ጋር ተያይዞ ለተነሳው ጥያቄ “ፌዴሬሽኑ ክለቦችን መደገፍ አለበት አዎ መደገፍ አለበት ድጋፍ ካላገኘን ግን እናፈርሰዋለን ካላችሁ መጀመሪያውኑ ክለብ ሊኖራችሁ አይገባም እንደ ፌዴሬሽን መደገፍ ሁለተኛና ሶስተኛ መሆን አለበት..ዋናው ግን ክለቦች ራስን መቻል አለባቸው ” ሲሉ መልሰዋል።
አንድ ተሳታፊ በሰጠው አስተያየት ” መንግስት እግርኳሱን መደገፍ አለበት ከፍተኛ በጀት ለስፖርቱ እየተበጀተ ለምን እግርኳሱ ይዘለላል….? ማስ ስፖርትን የሚደግፈው ካናዳ ነው እንዴ..? መንግስትም እግርኳሱን የግድ መደጎም አለበት..” በማለት የሰጠው አስተያየት ትኩረት የተቸረው ሆኗል።
የፌዴሬሽኑ ሃቃቤ ነዋይ አቶ አቶ ደመላሽ ደለለኝ በበኩላቸው “ስፖርቱን ለመምራት አደረጃጀቱ መስተካከል አለበት ጽ/ቤቱን ስንረከብ የተዘጋን በር ከፍተን ነው…ታግለናል በእናንተ በኩል ቅሬታ አቅርቦ መሄድ ብቻ ሳይሆን ማገዝ ይጠበቅባችኋል እንደ ፌዴሬሽን ውስጣዊ ውጫዊ ችግር ነበረብን እርስ በርስ ሆነ ከውጪ ሃይል ጋር ተፋልመናል ልታግዙን ይገባል ካልሆነ መጠቋቆም ምን ይረባል …? ስንረከብኮ ህጋዊ የፋይናንስ ገቢ ወጪ የለም ወደ ሃላፊነቱ ስመጣ አራተኛ አመቴ ነው አንድም ብር ያለ ምክንያት አልወጣም….
ከእኛ ጋር ጀምረው ያቆሙ አሉ እኛ የሰራነው ያላቆምነው ችግር ስለሌለ አይደለም እንደ ቀሩት ያልቀረነው የፕሬዝዳንቱ የአቶ የደረጄ አረጋ ጥንካሬ ታክሎበት ነው ለዚህም ማመስገን አለብን ከፋይናንስ አንጻር ስናይ አልተደገፍንም ከሌሎች ፌዴሬሽኖች አንጻር ወደኋላ ቀርተናል ሌሎቹ በመንግስት ይደጉማል ለኦሮሚያ 5 ሚሊዮን ብር ይደጎማል ከፍተኛ የሆነ የምዝገባ ገንዘብ ያስከፍላሉ … እዚህ ግን በተቃራኒው ነው በእውነት መንግስት ድጋፍ ማድረግ አለበት ከተደጎምን ስራው ቀላል ነው” በማለት አስተያየት ሰጥተዋል።
ጠቅላላ ጉባኤው የዘገየበትን ምክንያት አስመልክቶ በተሰጠ ምላሽ ” ከጉባኤውና ምርጫ እንደገና መካሄድ አለበት በሚል ከወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ጋር የተፈጠረው አለመግባባት እና የፌዴሬሽኑ ዋና ጸሃፊዎች ቅይይር መከሰቱ ለፌዴሬሽኑ ጉባኤ ቀን መዘግየት ምክንያት ሆኗል ተብሏል። ስለ ስፖንሰርሺፕ በተሰጠው አስተያየት በሶሻል ሚዲያ ያልተጨበጠ ወሬ እየተወራ ባለቀ ሰአት ወደ 2 ሚሊዮን ብር አጥተናል ሁላችንም ይህን መታገል አለብን ከተቋማት ጋር ተነጋግረን ተሳካ አለቀ ብለን ስንሄድ እክል እየገጠመን ተቸግረናል አሁንም ቢሆን ግን ተስፋ ሳንቆርጥ የምንችለውን እንጥራለን እናንተም አግዙን” “የሚል ምላሽ ተሰጥቷል።
በጉባኤው ዙሪያ ጠንካራ ማስገንዘቢያ የሰጡት የአዲስ አበባ ከተማ የወጣቶችና ስፖርትና ቢሮ የማህበራት ማደራጃ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አያሌው “ጠቅላላ ጉባኤ ትልልቅ አጀንዳ የሚነሱበት ነው ከዚያ ውጪ አሁን እንደታዘብኩት ጥናት ያሰፈልጋል የክለቦቹ መብትና ግዴታ ምንድነው..? የሚለው መታወቅ አለበት ክለብ ማለትስ ምንድነው ..? ብለን እንደ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ጠንካራ ስራ ነው የምንሰራው …አንድ ክለብ ላይሰንስ ካገኘ ትክክለኛ ክለብ መሆኑን ማረጋገጥ አለብን በቀጣይ የምናተኩርበት ይሆናል … ከድጎማና በጀት ጋር ተያይዞም ለክለቦች ድጋፍ ተብሎ የሚበጀት በጀት የለም ወደፊትም አይኖርም የከተማው የስፖርት ምክር ቤቱ የስፖርት ማዘውተሪያ፣ የሰው ሃይል ምደባና የታዲጊ ፕሮጀክትን ብቻ ይደግፋሉ ክለቦች ይህን ማወቅ አለባቸው .ከአትሌቲክስና እግር ኳስ ፌዴሬሽኖች ውጪ 10 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ለሌሎቹ ፌዴሬሽኖች ያደርጋል ሁለቱ ፌዴሬሽኖች ራሳቸውን ችለው ወጥተዋል… እግርኳስ ፌዴሬሽኑ ወደ ቢሮ ይመለስ ከተባለ በአመት 1 ሚሊዮን ብር ድጎማ ለመንግስት ቀላል ነው ለእግርኳሱ ግን አያዋጣም
ክለቦች በራሳቸው የሚቆሙበትን መንገድ መፈለግ እንጂ ድጎማን እንደዋና ባያደርጉት እመክራለሁ አዲስ አበባን ወክለው ለሚሄዱ ክለቦች 30 ሺህ ብር የሚደጎመው የስፖርት ምክር ቤቱ በሰጠው ውሳኔ ነው ያንሳል ከተባለ ግን ም/ቤቱ በድጋሚ የሚያየው ይሆናል” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
በጉባኤው ላይ በጎደለ አመራሮች ፋንታ በተካሄደው የምርጫ ሂደት ተመርጣ በቀረችው ማህሌት ሰለሞን ምትክ በተጠባባቂነት ተይዛ የነበረችው ረድኤት በአብላጫ ድምጽ ተተክታለች።
በዕለቱ ለካዲስኮ የቀለም ፋብሪካ፣ ለጌጅ ኮሌጅ ፣ ለፊያሜታ የግል ድርጅቶች አማካሪ የምስጋናና የዕውቅና ስነስርዓት ተካሂዷል። ጉባኤው ሲጠናቀቅ የዕለቱ የክብር እንግዳ የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ባህሩ ጥላሁን ” የአዲስ አበባ እግር ኳስን ለማሳደግ ስንተጋገዝ አብሮ ለመጓዝ ስንሰራ ኖረናል የልምምድ ልውውጥን አድርገናል በተደጋጋሚ በተለያየ ጉባኤ ላይ ተወካይ ልከን ስለ ጉባኤዎቹ ያለውን ሂደት መረጃ ስናገኝ ኖረናል የኳስ እጥረት ተከስቷል ለታዳጊና ለፕሮጀክት ድጋፍ ስናደርግ ቆይተናል…ጠቅላላ ጉባኤው እንደ ፊፋና ካፍ ጉባኤ ስታንዳርድ መካሄድ አለባቸው መድረኮች ሲመሩ ፕሬዝዳንትና ዋና ጸሃፊው ብቻ ናቸው ሌሎቹ መናገር አይጠበቅባቸውም የአዲስ አበባ እግርኳስ ደንብ የቢሮው እንደሆነ ሁሉ የኢትዮጵያና የካፍ የፊፋ ህጎች መተግበር አለበት … ክልሎች የየራሳቸው የስራ ሪፖርት ሲያቀርቡ አልነበረም ደንቡ ስታስተካክሉ ይህ ቢካተት ጥሩ ነው። ፌዴሬሽናችን አብሮ ለመስራት ዝግጁ ነው በቀጣይ ጠቅላላ ጉባኤያችሁ ከአጀንዳ ውጪ አይሁን ከመጣችሁበት ጉዳይ ውጪ አትውጡ በቀጣይ መልካም የስራ ዘመን ይሁንላችሁ” በማለት ተናግረዋል።
የመዝጊያ ንግግር ያደረጉት የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ደረጄ አረጋ “ለአዲስ አበባ እግርኳስ ፌዴሬሽን የጽ/ቤት ሰራተኞች፣የንኡሳን ኮሚቴ አባላት ባይኖሩ 134 ክለቦች ውድድርን በሰላም ማጠናቀቅ አይታሰብም ለዚህም አመሰግናልሁ ባለድርሻ አካላት እግርኳስ እንዲለወጥ የምታደርጉትን ጥረት ሁሉ እቀበላለሁ በጉዟችን መርከቡ ሲንገራገጭ አይ አብረን አለን ብላችሁ ስላደረጋችሁልን ድጋፍ ከልብ አመሰግናለሁ ፌዴሬሽኑና አቶ ባህሩ ጥላሁንን አመሰግናለሁ አብሮ ለመስራት የተገባውን ቃል ያከብራለሁ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ” በማለት የመዝጊያ ንግግራቸውን አጠናቀዋል።
ጉባኤዎው ሲጀመር በዚህ ሳምንት ህይወቱ ላለፈው ጋዜጠኛና ተንቀሳቃሽ ላይብረሪ ለነበረው ገነነ መኩሪያ/ሊብሮ/ የአንድ ደቂቃ የህሊና ጸሎት አድርጓል።