በመክፈቻው ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉባቸው ሁለት ውድድሮች ይካሄዳሉ።
ምሽት 3 ሰዓት ከ35 ላይ የሴቶች 1 ሺህ 500 ሜትር የማጣሪያ ውድድር የሚካሄድ ሲሆን፥ በማጣሪያ ውድድሩ ገንዘቤ ዲባባ፣ ጉዳፍ ፀጋዬ፣ በሱ ሶዶ እና ፋንቱ ወርቁ ይሳተፋሉ።
አትሌት ገንዘቤ ዲባባና አትሌት ፋንቱ ወርቁ በመጀመሪያው ምድብ፣ አትሌት ጉዳፍ ፀጋዬ በ2ኛው ምድብ፣ አትሌት በሱ ሳዶ በ3ኛው ምድብ ተደልድለው ውድድራቸውን ያካሂዳሉ።
- ማሰታውቂያ -
ከሶስቱ ምድብ ከእያንዳንዳቸው በደረጃ ከ1 እስከ 6ኛ የወጡ እንዲሁም ከሁሉም ምድብ 6 የተሻለ ሰዓት ያላቸው በአጠቃላይ 24 አትሌቶች ቅዳሜ ሐምሌ 29 2009 ዓ.ም ከምሽቱ 3 ስአት ከ35 ላይ ለሚካሄደው ግማሽ ማጣሪያ ያልፋሉ።
ምሽት 5 ሰዓት ከ20 ላይ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉበት የወንዶች 10 ሺህ ሜትር ውድድር ተጠባቂ ነው።
በውድድሩ ላይ አትሌት አባዲ ሀዲስ፣ ጀማል ይመር እና አንዱአምላክ በልሁ ኢትዮጵያን በመወከል ይወዳደራሉ።
እንግሊዛዊው ሞ ፋራህ ለኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ፈታኝ እንደሚሆን ነው የሚጠበቀው።
ቅዳሜ 4 ስአት ከ10 ላይ የ10 ሺህ ሜትር ሴቶች የፍፃሜ ውድድር የሚካሄድ ሲሆን፥ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ፣ አልማዝ አያና እና ደራ ዲዳ ኢትዮጵያን ይወክላሉ።
በዚህ ውድድር አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ እና አልማዝ አያና የሚያደርጉት ፉክክር ይጠበቃል።
የለንደን አትሌቲክስ ሻምፒዮና እሁድም ሲቀጥል ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉበት የወንዶች እና ሴቶች ማራቶን ውድድር ይካሄዳል።