የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከነገ(ቅዳሜ) ጀምሮ በቀጣዮቹ 4 ቀናት በሚካሄዱ ስምንት ጨዋታዎች ቀጥሎ ይውላል።በትግራይ ስታድየም ሚካሄደው የመቐለ 70 እንደርታ እና የፋሲል ከነማ ጨዋታ እንደሚከተለው ዳሰነዋል።
ጨዋታ: መቐለ 70 እንደርታ ከ ፋሲል ከነማ
የጨዋታ ቀን: ቅዳሜ ጥር 30/2012
የጨዋታ ሰዓት: 9:00
የጨዋታ አርቢትር: ኢንተርናሽናል አርቢትር በላይ ታደሰ
የጨዋታ ቦታ: ትግራይ ስታድየም
በሊጉ ደረጃ ሰንጠረዥ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ሁለተኛ እና ሥስተኛ ደረጃን የያዙት መቐለ 70 እንደርታና ፋሲል ከነማ የሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታቸውን በትግራይ ስታድየም ያካሂዳሉ።ሁለቱም ቡድኖች በነገው ጨዋታ ወደ ሊጉ መሪነት ሊያስጠጋቸው ሚችለውን ሥስት ነጥብ ለማግኘት ከፍተኛ ፋክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል።
- ማሰታውቂያ -
መቐለ 70 እንደርታዎች በ12ተኛው ሳምንት በጅማ አባጅፋር የተነጠቁትን ሥስት ነጥብ ለማካካስ ጨዋታውን አሸንፈው ለመውጣት አቅደው ወደ ሜዳ ሊገቡ እንደሚችሉ ይገመታል።እንደ አብዛኞቹ የኢትዮጲያ ፕሪምየር ሊግ ክለቦች በሜዳቸው ጥሩ ክብረወሰን ያላቸው መቐለ 70 እንደርታዎች በቀጥተኛ አጨዋወት በረጅሙ ከመሀል እና ከመስመር በሚነሱ ኳሶች እድሎችን ለመፍጠር ይሞክራሉ ተብሎ ይጠበቃል።አሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ የተለያዩ ቦታዎችን በመሸፈን የቡድኑ ወሳኝ ተጨዋች የሆነውን ያሬድ ከበደን በጉዳት ማጣታቸው የነገውን ጨዋታ ከባድ ሊያደርግላቸው ይችላል።ምዓም አናብስቶቹ ከጨዋታው ሙሉ ሥስት ነጥብ ለማግኘት ፊት ላይ አማኑኤል ገብረሚካኤል እና ኦኪኪ ኦፎላቢ ላይ መሰረት ያደርገ የማጥቃት ስልትን መርጠው ሊገቡ እንደሚችሉ መገመት ከባድ አይሆንም።
ባሳለፍነው ሳምንት በሜዳቸው አፄ ፋሲለደስ ወልዋሎን ያሸነፋት ፋሲሎች በዘንድሮው የኢትዮጲያ ፕሪምየር ሊግ ከሜዳቸው ውጪ እየታየባቸው ሚገኘውን ደካማ አቋም ለማስተካከል ቢያንስ ከዚህ ጨዋታ ነጥብ ማግኘት ግድ ሚላቸው ይሆናል።የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ወስደው መጫወትን ሚመርጡት አፄዎቹ በነገው ጨዋታ ኳስን ከኃላ ለመመስረት በሚሞክሩበት ጊዜ ሚፈጥሩዋቸውን ስህተቶች መቀነስ ግድ ሚላቸው ይሆናል።በተጨማሪ ከኃላ የሚጀመሩት ኳሶች በሜዳው የመጨረሻ ክፍል ላይ ደርሰው ግብ ሊሆኑ የሚችሉ እድሎች እንዲፈጠሩ መሀል ላይ ሚሰለፋት ሱራፋኤል ዳኛቸውና በዛብህ መለዮ የቡድኑ የማጥቃት ሽግግር ላይ ከፍተኛ ሀላፊነት ሚጠብቃቸው ይሆናል።
በነገው ተጠባቂ ጨዋታ መቐለ 70 እንደርታዎች ያሬድ ከበደን በጉዳት ሲያጡ አፄዎቹ በበኩላቸው የአማካያቸው ጋብርኤል አህመድን ግልጋሎት ማያገኙ ይሆናል።