የሀዋሳ ከተማ ስፖርት ክለብ አሰልጣኝ ውበቱ አባተ እና
ም/አሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረት እንዲሁም የቡድን መሪው አለምባንተ ማሞ ላይ በስልክ በደረሳቸው ማስፈራሪያና ዛቻ ከ2 ቀናት በፊት ክለቡን ለቀው ከሀዋሳ ወደ አዲስአበባ ቤተሰቦቻቸውን ይዘው መግባታቸው እየተነገረ ሲሆን ትናንት በም/አሰልጣኙ ሙሉጌታ ምህረት መኖሪያ ቤት ላይ ጥቃት መፈፀሙን ሀትሪክ ስፖርት ከምንጮቿ አረጋግጣለች፡፡
የችግሩ መንስኤ በ25ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ኘሪሚዮር ሊግ ሀዋሳ ከተማ በሜዳው ሲዳማ ቡናን ያስተናገደበትና በጨዋታው 1-1 በሆነ ውጤት ነጥብ የተጋሩበት የደቡብ ደርቢ እንደሆነና በዕለቱ ሀዋሳዎች የሲዳማ ቡናው አጥቂ አዲስ ግደይ 5 ቢጫ ካርድ አይቷል፡፡በመሆኑም ጨዋታው ሊያልፈው ይገባል በሚል ከጨዋታው መጀመር አስቀድመው ያስያዙት ክስ እንደሆነም ተነግሯል፡፡ነገር ግን 24ኛው ሳምንት ሲዳማ ቡና በሜዳው አዳማ ከተማን አዲስ ግደይ በ75′ ባስቆጠራት ብቸኛ ግብ 1-0 በረታበት ጨዋታ ይሄው ተጨዋች መጫዎት አልነበረበትም በሚል አዳማ ከተማ ለእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ያስገባው ይግባኝ ተቀባይነት አግኝቶ አዳማ ከተማ በፎርፌ ሶስት ነጥብና ሶስት ጎል ማግኘቱ እና ሲዳማዎች የፎርፌ ተሸናፊ መሆናቸው ይታወቃል፡፡
ከወራጂ ቀጠናው በ6 ነጥብ እርቀት በ34 ነጥብ በደረጃ ሰንጠረዡ 8ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡት ሀይቆቹ ሀዋሳ ከተማዎች በክለቡ ያጋጠማቸው ያልጠበቁት ችግር አለመረጋጋት ውስጥ ከመግባታቸው ባለፈም በመጠናቀቅ ላይ ባለው እና 4 ጨዋታዎች በቀሩት የኢትዮጵያ ኘሪሚዮር ሊግ ጨዋታቸውን በጥሩ ስነ ልቦና እንዳያደርጉ ጫና እንደፈጠረባቸው እና ክለቡ በ27ኛው ሳምንት በሜዳው ከኢትዮጵያ ቡና ጋር ለሚያደርጉት ወሳኝ ጨዋታ ቡድኑ በግብ ጠባቂ አሰልጣኝ አምጣቸው ሀይሌ እየተመራ ዝግጅት
በማድረግ ላይ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከላይ የቀረበውን ዘገባ ትክክለኛነት ለማረጋገጥ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከተው አሰልጣኝ ውበቱ አባተ ተንቀሳቃሽ የእጅ ስልክ ላይ በመደወል ለማረጋገጥ ሞክረን አሰልጣኙ በወቅቱ ምላሽ መስጠት ባለመቻሉ በእሱ በኩል ያለው ምላሽን በዘገባው ለማካተት አልቻልንም። ለአንባቢዎቻችን የተማላ መረጃ ለማቅረብ በሚል በተመሳሳይ ረዳት አሠልጣኙ ሙሉጌታ ምህረትና ከክለቡ ሀላፊዎች ትክክለኛውን መረጃ ለማግኘት ያደረግነው ጥረት ሊሳካልን አልቻለም።በጉዳዩ ዙርያ ምላሽ መስጠት የሚፈልግ አካል ካለ በደስታ የምናስተናግድ መሆኑን እንገልፃለን።