የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ክፍያ ፋይናንሻል ቴክኖሎጂ ኃ/የተ/የግ/ማህበር ከተባለ ሀገር በቀል ተቋም ጋር በመተባበር የኢ-ትኬት አገልግሎት ለመስጠት ቅድመ ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን ዛሬ በካፒታል ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ተገልጿል፡፡
በመግለጫው የኢ-ትኬት አግልግሎት ሽያጭ ሲጀምር የኢትዮጵያን እግር ኳስን የቆየና የተንዛዛ የቲኬት አገልግሎት ሽያጭ አሰራር በማሻሻል በዘመናዊ የኢ-ትኬት አገልግሎት በመቀየር የስፖርት ቤተሰቡን ጊዜና ወጭ ያገናዘበ ፈጣንና ቀልጣፋ፡ጥራት ያለው አገልግሎት ለማቅረብ ያስችላልም ተብሏል፡፡ ከዚህም ቀደም የስታዲዬም መግቢያ ትኬት ለመግዛት ይወስድ ከነበረው ጊዜ እና ወጭ ባሻገር የስፖርት ቤተሰቡን እንግልት ችግር እንደሚቀርፍ የተነገረለት የኢ-ቲኬት ሽያጭ ከሚያዚያ 25/2010 ዓ/ም ጀምሮ አገልግሎቱ በይፋ እንደሚጀምር ተነግሯል፡፡
ከዚህ ቀደም የስፖርት ቤተሰቡ የስታዲየም የመግቢያ ቲኬት ለመግዛት በጨዋታው ዕለት ይወስድበት የነበረውን ጊዜና ወጭ ለመቆጠብ፡በስታዲየሙ ዙሪያ አልፎ አልፎ የሚታዩትን ሰልፎች በማስቀረት አገልግሎት አሰጣጡን የተሳለጠ ለማድረግ በማንኛውም ጊዜና ቦታ የኢ- ቲኬት አገልግሎት “የኔ ትኬት”የሚል አገልግሎት በ13ቱም የስታዲየም በሮችና በከተማዋ በተመረጡ ቦታዎች አገልግሎቱን ከሚያቀርቡ ድርጅቶች በተጨማሪ የባንክ ሂሳብ ደብተር ላይ ባለ ገንዘብ በሞባይል መተግበሪያ የመግቢያ ቲኬት ከጨዋታው አስቀድሞ ባሉ በማንኛውም ቀናት መግዛት ይቻላል፡፡በጨዋታው ቀን ወደ ስታዲዬም ሲገቡ የገዙትን የኢ-ቲኬት ‘በዘመናዊ ሪደር” በማስነበብ መግባት የሚችሉበትን ቴክኖሎጂና የመሰረተ ልማት አውታር ዝርጋታ መጠናቀቁ ይፋ ተደርጓል፡፡
“የኔ ትኬት”አገልግሎት የማንኛውንም ጨዋታ የተሰበሰበ ገንዘብ በ48 ሰዓት ውስጥ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አውቶማቲክ በሆነ መልኩ የማስተላለፍ አቅም ያለው ቴክኖሎጂ ሲሆን በተጨማሪም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሚቆረጡ ትኬቶችን ቢሮ ሁኖ መመልከት የሚያስችለው የዳሽቦርድ ቴክኖሎጂንም ያካተተ ነው፡፡በተጨማሪም ከገዙት ትኬት የስታዲየም ክፍል ውጭ ተመልካች ወደ ሌላ ክፍል ለመግባት የሚደረግ ጥረትን ጥቆማ እንደሚሰጥም ተነግሯል፡፡በአዲስ አበባ ስታዲዬም እስከ 25ሺ ትኬቶች እንደሚሸጡም ታውቋል፡፡
- ማሰታውቂያ -
ከዚህም ባሻገር አገልግሎቱን የተሳለጠ ለማድረግ የስፖርት ቤተሰቡ የሚያነሳቸውን ጥያቄዎች ለመመለስና በቅርበት ለመገናኘት በ8586 በአራት ቋንቋዎች በአማርኛ፡ኦሮሞኛ፡ትግርኛና እንግሊዘኛን ያቀፈ በቀን ለ12 ሰዓታት አገልግሎት የሚሰጥ የደንበኞችን አገልግሎት ያቀፈ ነው፡፡
የኢ-ትኬት አገልግሎት ሽያጭ በአዲስአበባ ስታዲዮም ብቻ እንደሚተገበርና ትልቅ ጨዋታዎች ሲኖሩ አገልግሎቱ እንደሚሰጥ የተነገረ ሲሆን በቀጣይ በተለያዩ የክልል ስታዲዬሞች ይሄው አገልግሎት እንደሚተገበር ተነግሯል፡፡