አትሌት ጫላ በዩን ለሁለት ዓመት ከማንኛውም የአትሌቲክስ ስልጠና እና ውድድር ተሳትፎ ማገዱን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ገለጸ።
አትሌት ጫላ በዩ የ3ሺህ ሜትር መሰናክል ተወዳዳሪ ሲሆን በለንደኑ የዓለም አትሌቲክስ ውድድር አልተመረጥኩም በሚል ነበር ማክሰኞ ሐምሌ 18 ቀን 2009 ዓ.ም በአሰልጣኙ ሻምበል ዮሃንስ መሀመድ ላይ የድብደባ ጥቃት የፈጸመው።
አትሌቱ ጥቃት ካደረሰ በኋላ ወደ ጫካ ማምለጡ ተገልጿል።
በጉዳዩ ዙሪያ ትናንት አስቸኳይ ስብሰባ ያደረገው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አትሌት ጫላ በዩ በሰራው ያልተገባ ድርጊት የሁለት ዓመት እገዳ መጣሉን ያስታወቀው።
- ማሰታውቂያ -
በ2003 ዓ.ም በጸደቀው የፌዴሬሽኑ ደንብና መመሪያ አንቀጽ 15 ቁጥር ሁለት መሰረት ከፍተኛ የዲስፕሊን ጉድለት የፈጸመ አትሌት በሁለት አመትና ከዛ በላይ ከማንኛውም ስልጠናና ውድድር ይታገዳል ይላል።
ስራ አስፈጻሚውም በጉዳዩ ዙሪያ በስፋት ከመከረ በኋላ አትሌቱን ለሁለት አመት ከማንኛውም የአትሌቲክስ ስልጠና እና ውድድር እንዲታገድ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል።
በተጨማሪ በአትሌቱ ላይ የተጀመረው የወንጀል ክስ በፖሊስ አካላት ተጣርቶ የሚታወቅ መሆኑን ፌዴሬሽኑ አስታውቋል።
ይህ ዜና እስከተጠናከረበት ጊዜ ድረስ አትሌቱ አስካሁን በቁጥጥር ስር አለመዋሉን የፌዴሬሽኑ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ስለሺ ብስራት ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ተናግረዋል።
ፌዴሬሽኑ ከአንድ ሳምንት በኋላ በእንግሊዝ ለንደን በሚደረገው 16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከ800 ሜትር እስከ ማራቶን ርቀቶች ኢትዮጵያን የሚወክሉ 40 አትሌቶችን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም።