21ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬም ቀጥሎ ሲያመሽ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ድል ተመልሷል።
በአዲስ አበባ ስታዲየም ሊጉን መምራት ጀምሮ የነበረውን ሲዳማ ቡና ያስተናገደው ቅዱስ ጊዮርጊስ ሳላዲን ሰይድ ባለቀ ሰአት ባስቆጠራት ብቸኛ ግብ ነው ማሸነፍ የቻለው።
- ማሰታውቂያ -
በዚህም ከስድስት አመታት በኋላ ሁለት ተከታታይ ሽንፈት ያስተናገዱት ፈረሰኞቹሊጉን በ38 ነጥብ መምራት ጀምረዋል።
የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በመብራት መጥፋት ምክንያት ለተወሰኑ ደቂቃዎች ተቋርጦ ቆይቷል።
9 ሰአት ላይ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር የተጫወተው ደደቢት ደግሞ 1 ለ 1 በሆነ ውጤት አቻ ተለያይቷል።
ብርሃኑ ቦጋለ ጨዋታው በተጀመረ በ3ኛው ደቂቃ ደደቢትን ቀዳሚ ያደረገች ግብ ቢያስቆጥርም ኢብራሂም ፎፋና ኢትዮ ኤሌክትሪክን አቻ አድርጓል።
ሊጉ ነገም ሲቀጥል ኢትዮጵያ ቡና ከወላይታ ዲቻ 11 ሰዓት ከ30 ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ።
ፕሪሚየር ሊጉን ቅዱስ ጊዮርጊስ በ38 ነጥብ ሲመራ፣ ደደቢት እና ሲዳማ ቡና በእኩል 36 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ተከታዩን ደረጃ ይዘዋል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና አዲስ አበባ ከተማ በእኩል 16 ነጥብ በደረጃው ግርጌ ላይ ተቀምጠዋል።
ኮከብ ግብ አግቢነቱን ጌታነህ ከበደ በ16 ጎሎች የሚመራ ሲሆን፥ ሳላዲን ሰይድ በ10፣ አዳነ ግርማ እና ፍፁም ገብረማርያም በ9 ጎሎች ይከተላሉ።