በ20ኛው ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ በተደረገው የመጀመሪያ ጨዋታ ወላይታ ድቻ እና ሰበታ ከተማ ያለ ምንም ግብ ተጠናቋል ።
ወላይታ ድቻ በ19ኛው ሳምንት ጨዋታ በኢትዮጵያ ቡና በተሸነፉበት ጨዋታ በነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ ላይ ምንም ለውጥ ሳያደርጉ የገቡ ሲሆን በሰበታ ከተማ በኩል ደግሞ በሳምንቱ በሲዳማ ቡና 3 – 0 በተረቱበት ጨዋታ ከነበረው ምርጥ 11 ሶስት ለውጦችን በማድረግ በአለማየሁ ሙለታ ፤ ቢያድግልኝ ኤልያስ እና በፍፁም ገብረማርያም ምትክ ጌቱ ሀይለማርያምን ፤ ጋብሬል አህመድ እና ሳሙኤል ሳሊሶን ተክተው ገብተዋል ።በጨዋታው የመጀመሪያ ደቂቃዎች ላይ ሰበታ ከተማዎች በወላይታ ድቻ ላይ ጫና ፈጥረው መጫወት የቻሉበት ነበር ። በወላይታ ድቻ በኩል ግን በራሳቸው ሜዳ ላይ በርከት ብለው የሰበታ ከተማን የማጥቃት እንቅስቃሴ በማቋረጥ እና በረጃጅም ኳሶች ወደ ፊት ለመድረስ ጥረቶች ለማድረግ የሞከሩበት ነበር ።
በሰበታ ከተማ በኩል በተለይም ከቆሙ ኳሶች እና ከሳጥን ውጪ በሚደረጉ ሙከራዎች የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ሞክረዋል ። በ7ኛው ደቂቃ ላይ ሳሙኤል ሳሊሶ ከርቀት አክርሮ የመታው ኳስ እና በአንተነህ ጉግሳ ተጨርፎ ለጥቂት የወጣው ኳስ ተጠቃሽ ነው ።
በወላይታ ድቻ በኩል በ21ኛው ደቂቃ ላይ ምንይሉ ወንድሙ ከሳጥን ውጪ ሞክሮ ለጥቂት ከግቡ አናት በላይ የወጣው ኳስ የመጀመሪያ ሙከራ ነበር ።
- ማሰታውቂያ -
ከውሀ እረፍት በኋላ ወላይታ ድቻዎች በተወሰነ መልኩ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረቶችን ያደረጉበት ነበር ። በዚህም 34ኛው ደቂቃ ላይ በያሬድ ዳዊት አማካኝነት ያደረጉት የግብ ሙከራ በምንተስኖት አሎ ሲመለስ አበባየሁ አጪሶ ከሳጥን ውጪ ያደረገው የግብ ሙከራም ኢላማውን ሳይጠብቅ ቀርቷል ።በ43ኛው ደቂቃ ላይ ቃልኪዳን ዘላለም ከግራ መስመር ለምንይሉ ወንድሙ የቀነሰለትን ኳስ ምንይሉ ሳይደርስብት ቀረ እንጂ ለጦና ንቦቹ ቀዳሚ ግብ የማስቆጠሪያ ጥሩ ዕድል ነበር ።
በሁለተኛው አጋማሽ የጦና ንቦቹ በተሻለ የጨዋታ ብልጫ በመውሰድ መጫወት የቻሉበት ነበር ። በተለይም በቀኝ መስመር በኩል ባደላው የማጥቃት እንቅስቃሴያቸው የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ችለው ነበር ።
በሰበታ ከተማ በኩል በመጀመሪያው አጋማሽ 20ዎቹ አጋማሽ ደቂቃ ላይ የነበራቸውን የበላይነት ይዘው መቀጠል ሳይቸሉ ቀርተዋል ።
በ55ኛው ደቂቃ ላይ አብዱልሀፊዝ ቶፊቅ ከሳጥን ውጪ ያደረገው ሙከራ ኢላማውን ሳይጠብቅ ቀርቷል ። በ63ኛው ደቂቃ ላይ በጦና ንቦቹ በኩል ምንይሉ ወንድሙ ከቀኝ መስመር አቅጣጫ ወደ ግብ ክልል ያሻገረው ኳስ በቀጥታ ወደ ግቡ ሄዶ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂው ምንተስኖት አሎ ይዞታል ።
ከነዚህ ሙከራዎች በኋላ ቀጣዩን የግብ ዕድል ለመመልከት እስከ 81ኛው ደቂቃ መጠበቅ የግድ ብሎ ነበር ። በተጠቀሰው ደቂቃ ላይ አበባየሁ አጪሶ ከሳጥን ውጪ በግራ እግሩ አክርሮ የመታው ኳስ በምንተስኖት ተመልሶ የማዕዘን ምት ሆኗል ።መደበኛው የጨዋታ ክፍለጊዜ ሊጠናቀቅ ሶስት ያህል ደቂቃዎች ሲቀሩት የጦና ንቦቹ በተከታታይ ሁለት ጥሩ የሆኑ የግብ ሙከራዎችን ማድረግ ቢችሉም ምንተስኖት የሚቀመስ አልነበረም ። ያሬድ ዳዊት ከቀኝ መስመር አቅጣጫ ወደ ሳጥን ይዞ የገባው ኳስ ለምንይሉ ወንድሙ ደርሶ ምንይሉ ወደ ግብ የላከው ኳስ በግብ ዘቡ ሲመለስ በቅርብ የነበረው ቃልኪዳን ዘላለም ዳግም ወደ ግብ የመታው ኳስም በምንተስኖት አሎ ተመልሶ ወጥቷል ።
በመጨረሻም ሁለቱም ቡድኖች ያለምንም ግብ ባጠናቀቁት ጨዋታ አንድ አንድ ነጥቦችን ይዘው መውጣት ችለዋል ።
ውጤቱን ተከትሎ ወላይታ ድቻ ነጥቡን 34 በማድረስ በጊዜያዊነት ወደ 2ኛ ደረጃ ከፍ ያለ ሲሆን ሰበታ ከተማ ደግሞ ነጥቡን 13 ማድረስ የቻለ ቢሆንም በደረጃው ላይ ግን ለውጥ ሳያደርግ 19ኛ ደረጃ ላይ ለመቆየት ተገዷል ።
በ21ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ወላይታ ድቻ በመጪው ሚያዝያ 24 ( ሰኞ ) አመሻሽ 12 ሰዓት ጀምሮ ፋሲል ከነማን ሲገጥም ሰበታ ከተማ ደግሞ አንድ ቀን ቀደም ብሎ ሚያዝያ 23 ( ዕሁድ ) በተመሳሳይ ሰዓት ከድሬዳዋ ከተማ ይጫወታል ።