በሀያ ሶስተኛዉ ሳምንት ሁለተኛ ዕለት ቀዳሚ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን ሀምበሪቾ ዱራሜን ሁለት ለዜሮ በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል።
ጥቂት የሚባል የግብ ሙከራ በተስተዋለበት የሁለቱ ክለቦች የመጀመሪያ አጋማሽ ኢትዮጵያ መድኖች በአጠቃላይ የጨዋታዉን ብልጫ ሲወስዱ ፤ በተቃራኒው በእንቅስቃሴ ረገድ ብልጫ ተወስዶባቸዉ የነበሩት ሀምበሪቾ ዱራሜዎች ደግሞ በአጋማሹ ተጠቃሽ ሙከራም ለማድግ ሲቸገሩ ተስተውሏል። በዚህ ሁኔታ በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ጀሮም ፍሊፕ በሀምበሪቾ ዱራሜ በኩል ቀዳሚ ሙከራ አድርጎ የነበረ ቢሆንም የግብ ዘቡ ፓሉማ ፓጂ ግን በግሩም ቅልጥፍና ኳሷን መልሷል።
ተደጋጋሚ ዕድሎች ማግኘት የቀጠለዉ ኢትዮጵያ መድን በቅርቡ ክለቡን በተቀላቀለዉ የአጥቂ ስፍራ ተጫዋች አብዱሳ ጀማል አማካኝነት ድንቅ ሙከራ ማድረግ ቢችልም ነገር ግን አሁንም የግብ ዘቡ ኳሷን በግሩም ብቃት መልሷል። በአብዛኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ወደ ራሳቸዉ የግብ ክፍል አፈግፍገዉ በተደራጀ መከላከል በመጫዎት የተጋጣሚን ቡድን ማጥቃት በመመከት እና አልፎ አልፎ ደግሞ በመልሶ ማጥቃት አደጋ ለመፍጠር ሲጥሩ የነበሩት ሀምበሪቾዎች ይህ ነዉ የሚባል ተጠቃሽ ሙከራ ሳያደርጉ አጋማሹ ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
በሁለተኛዉ አጋማሽ ኢትዮጵያ መድን ጥሩ በመንቀሳቀስ እና ብልጫ በመዉሰድ የተሻለ የነበረ ሲሆን ፤ በሙከራ ረገድ ግን ሀምበሪቾዎች በአላዛር አማካኝነት ድንቅ ሙከራን ማድረግ ችለዉ ነበር ። በ68ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግን አጥቂዉ ወገኔ ገዛኸኝ ያሻገረዉን ኳስ አቡበከር ሳኒ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን ኢትዮጵያ መድንን መሪ ማድረግ ቻለ ።
ከግቧ መቆጠር በኋላ በተደጋጋሚ ጫና ፈጥረዉ መጫወት የቻሉት መድኖች በ75ተኛዉ ደቂቃ ላይ አቡበከር ሳኒ ከአለን ካይዋ የተሻገረለትን ኳስ የግብ ጠባቂዉ ስህተት ታክሎበት ወደ ግብነት በመቀየር የክለቡን ሁለተኛ ግብ አስቆጥሮ ጨዋታዉ በኢትዮጵያ መድን ሁለት ለዜሮ አሸናፊነት ተጠናቋል።
ኢትዮጵያ ቡና ሁለት ለዜሮ ከመመራት ተነስቶ ከሊጉ መሪ ንግድ ባንክ ጋር ሁለት አቻ ተለያይቷል ።
በተመጣጣኝ የጨዋታ እንቅስቃሴ በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ገና በ5ተኛዉ ደቂቃ አማካዩ ባሲሩ ዑመር በቀኝ መስመር በኩል ለሚገኘዉ ሱሉይማን ሀሚድ ያቀበለዉን ኳስ ተጫዋቹ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷን የግቡ አግዳሚ ሲመልስ ያኔ አጥቂዉ ሲሞን ፒተር አስቆጥሮ ክለቡን ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሪ ማድረግ ችሏል።
በመጠኑም ቢሆን የጨዋታ ብልጫ ተወስዶባቸዉ የነበሩት ነገር ግን በሙከራ ረገድ የተሻሉ የነበሩት ቡናማዎቹ በቀኝ መስመር በኩል በ9ነኛዉ ደቂቃ አብዱልከሪም ወርቁ ከኋላ ያገኘዉን ኳስ ገፍቶ ሳጥን ውስጥ ከገባ በኋላ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም የግቡ ቋሚ ኳሷን መልሷታል። በድጋሚም በ14ተኛዉ ደቂቃ አማካዩ አብዱልከሪም በአራት የንግድ ባንክ ተጫዋች መሐል ወደ ግብ የሞከረዉን ኳስ ግብ ጠባቂዉ ፍሬዉ ጌታሁን መልሷል።
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታም ከቀኝ መስመር በኩል አማኑኤል ዮሐንስ ከሌላኛዉ አማኑኤል አገኘዉ የተሻገረለትን ኳስ በጭንቅላቱ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ግብ ጠባቂዉ ፍሬዉ ጌታሁን እንደምንም ኳሷን አዉጥቷል። በ43ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግን ባንኮች ሁለተኛ ግብ አግኝተዋል። በዚህም ከግራ መስመር በኩል ፉዓድ ፈረጃ ወደ ሳጥን ያሻገረዉን ኳስ ሳይመን ፒተር በጭንቅላቱ ወደ ግብነት ቀይሮ የክለቡን መሪነት ወደ ሁለት ከፍ ማድረግ ቢችልም ፤ ነገር ግን ተጫዋቹ በጉዳት ምክንያት ተቀይሮ ወጥቷል።
ከዕረፍት መልስ ሁለቱም ክለቦች የተጫዋች ለዉጥ በማድረግ ጨዋታዉን ለመቆጣጠር ሲጥሩ ነገር ግን በአጋማሹ በሙከራ ረገድ የተቀዛቀዘ እንቅስቃሴን ሲያስመለክተን ፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንኮች ያስቆጠሩትን ግብ አስጠብቀዉ በይበልጥ ደግሞ ጨዋታዉን ለመቆጣጠር ሲጥሩ ፤ በቡናማዎቹ በኩል ደግሞ ግቦችን ለማግኘት ቶሎ ቶሎ ወደ ሶስተኛዉ የሜዳ ክፍል በመድረስ ዕድሎችን ለመፍጠር ሰመጥሩ ተስተውሏል።
በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታም በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ላይ እጅጉኑ ጫና ወስደዉ የተጫወቱት ቡናማዎቹ በ84ተኛዉ ደቂቃ ላይ ወደ ጨዋታዉ የሚመልሳቸውን ግብ አግኝተዋል ፤ በዚህም ከቀኝ መስመር በኩል አማካዩ አማኑኤል ዮሐንስ ከአስራት ቱንጆ የተቀበለዉን ኳስ ከሳጥን ዉጭ ወደ መትቶ ጎል ማስቆጠር ችሏል።
በዚህ ሂደት ተፋፍሞ በቀጠለዉ ጨዋታ በጭማሪው 90+2 ደቂቃ ላይም ከኋላ መስመር የተሻገረዉን ኳስ አንተነህ ተፈራ ለመስፍን ታፈሰ አቀብሎት ተጫዋቹ ደግሞ በሚደንቅ ሁኔታ ኳሷን እንደምንም ብሎ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡ ወሳኝ አንድ ነጥብ እንዲያገኝ አስችሎ ጨዋታው ሁለት አቻ በሆነ ዉጤት ተጠናቋል።