በሁለተኛዉ ዙር የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመክፈቻ ጨዋታ ባህርደር ከተማ እና ኢትዮጵያ መድን መርሐግብራቸዉን ያለ ግብ በአቻ ዉጤት አጠናቀዋል ።
ቀን 10 ሰዓት ሲል በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ኤፍሬም ደበሌ መሪነት መከናወን በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ የጣና ሞገዶቹ በመጀመሪያዎቹ ደቂቃዎች ላይ ብልጫ ያሳዩ ሲሆን ፤ በሙከራም ረገድ ገና በ10ኛዉ ደቂቃ ላይ ተከላካዮ ያሬድ ባየ ከርቀት ሙከራ ሲያደርግ ግብ ጠባቂዉ አቡበከር ኑራ ይዞበታል።
ተመጣጣኝ የጨዋታ እንቅስቃሴ እያስመለከተን በቀጠለዉ መርሐግብር በ31ኛዉ ደቂቃ ላይ በባህርዳር ከተማዎች በኩል በሀብታሙ ታደሰ አማካኝነት ሙከራ ሲደረግ ፤ በድጋሚ በ34ተኛዉ ደቂቃ ላይ ደግሞ መድኖች ወሳኝ ሙከራ ማድረግ ችለዋል ። በዚህም አቡበከር ወንድሙ ከግራ መስመር በኩል ያሻማዉን ኳስ ብሩክ ሙሉጌታ ሲሞክር ኳሱ ለጥቂት ወጥቷል።
- ማሰታውቂያ -
በመጨረሻዎቹ 20 ደቂቃዎች ላይ ጫና ፈጥረዉ መጫወት የቀጠሉት ባህርዳሮች በ70ኛዉ ደቂቃ ላይ ከግራ መስመር በኩል ከአጥቂዉ ሙጅብ ቃሲም የተቀበለዉን ኳስ እየገፋ የተጋጣሚ ቡድን ሳጥን ውስጥ መግባት የቻለዉ ቸርነት ኳሱን በቀጥታ ወደ ግብ ቢሞክርም የግብ ዘቡ አቡበከር ኑራ አምክኖታል። ከደቂቃዎች በኋላ ደግሞ በድጋሚ ጫናቸዉን ጨምረዉ የቀጠሉት የጣና ሞገዶቹ ተቀይሮ በገባዉ አማካዩ ፍሬዉ ሰለሞን አማካኝነት በ ደቂቃ እና በ ደቂቃ ላይ በተከታታይ ድንቅ ሙከራዎችን ማድረግ ቢችልም አንዱን አቡበከር ወንድሙ ተደርቦ ሲመልስ ሁለተኛዉን ደግሞ አቡበከር ኑራ አዉጥቶበታል።
በ77ተኛዉ ደቂቃ ላይ መድን ግብ ለማስቆጠር ተቃርበዉ ነበር ፤ በዚህም መሐመድ ግብ ጠባቂዉን አታሎ ካለፈ በኋላ ኳሷን ወደ ግብ ቢልክም ኢላማዋን ሳትጠብቅ ለጥቂት ወጥታለች። ከዚች አስቆጭ ሙከራ በኋላ በሁለቱ ክለቦች መካከል ድንቅ ፉክክር ተደርጎ መርሐግብሩ ያለግብ በአቻ ዉጤት ተጠናቋል።