በኢትየጵያ ፕሪምየር ሊግ ቅዳሜ ጥቅምት 25 ሊደረግ ቀጠሮ ተይዞለት ነገር ግን በብሔራዊ ቡድኑ(በዋልያዎቹ) የቻን ጨዋታ ምክንያት ወደ ዛሬ(ሰኞ) ተዛውሮ የነበረው እና በአዲስ አበባ ስታዲየም የተካሄደው የደደቢት እና የወላይታ ድቻ ጨዋታ ያለምንም ግብ 0-0 ተጠናቋል። በጨዋታው ላይ ወላይታ ድቻ በ3-5-2 አሰላለፍ ወደሜዳ ሲገቡ በአንጻሩ ደደቢት 4-4-2 አሰላፍ ይዞ መግባት ችሏል፡፡
ብዙም ፉክክር እና አዝናኝ ጨዋታ ባልተስተዋለበት በዚህ ጨዋታ 50ኛው ደቂቃ ላይ የደደቢቱ አጥቂ ጌታነህ ከበደ አክርሮ የጎሉ አንግል ጠርዝ ላይ የመታው ኳስ የወላይታ ድቻው ግብ ጠባቂ ፌቮ በድንቅ ሁኔታ ያወጣበት እና በወላይታ ድቻ በኩል ጃኮ አራፋት የመታው ኳስ የግቡን ብረት ለትሞ የመለሰበት የሚጠቀሱ ብቸኛ ጥሩ ሙከራዎች ናቸው፡፡
በፕሪምየር ሊጉ ከተደረጉት አምስት ጨዋታዎች ውስጥ ሶስቱ በአቻ ውጤት ሲጠናቀቁ ወልድያ ከተማ እና ጅማ አባጅፋር ባለድል በመሆን 3 ነጥቦች በማስመዝገብ የሊጉ መሪ መሆን ችለዋል። በእነዚህ አምስት ጨዋታዎችም 8 ግቦች ከመረብ ማረፍ ችለዋል።
ፕሪምየር ሊጉ ነገ ማክሰኞ ሲቀጥል 11:30 ላይ ኢትዮ-ኤሌክትሪክ ከ መከላከያ የሚጫወቱ ይሆናል።