በዕለቱ ቀዳሚ ጨዋታ በአስራ አራተኛዉ ሳምንት መርሐግብር ከወላይታ ዲቻ ጋር አንድ አቻ ተለያይቶ የነበረዉ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሲዳማ ቡናን በተከላካዩ አማኑኤል ተርፉ ብቸኛ ግብ 1ለ0 በሆነ ዉጤት አሸንፏል።
በሁለቱ ክለቦች ተመጣጣኝ የሚባል የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ መካሄድ በጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ገና በመባቻዉ ሙከራ ተደርጎበታል ። በዚህም በ10ኛዉ ደቂቃ ላይ ብርሃኑ በቀለ ከቀኝ መስመር በኩል ወደ ግብ ክልል የላካት ኳስ የግቡን አናት ገጭታ ስትወጣ በተመሳሳይ ይሄዉ ተጫዋች በ15ተኛዉ ደቂቃ ወደ ሳጥን የላካትን ኳስ ጊት ጋት ኩት ወደ ወደ ግብ ሞክሮ ኳሷ ለጥቂት ወጥታለች። በመጀመሪያው አጋማሽ ምንም እንኳን በጨዋታ ረገድ የተሻሉ የነበሩ ቢሆኑም ነገር ግን ኢላማዉን የጠበቀ ሙከራ ለማድረግ ተቸግረዉ የነበሩት ፈረሰኞቹ በመሐል በአጥቂዉ ሞሰስ ኦዶ አማካኝነት ካደረጉት ተጠቃሽ ሙከራ ውጭ ዕድል መፍጠር ሳይችሉ የመጀመሪያዉ አጋማሽ ተጠናቋል።
ከዕረፍት መልስ የማጥቃት ሀይላቸውን አጠናክረዉ የቀጠሉት ፈረሰኞቹ በ53ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ ማስቆጠር ችለዋል ። በዚህም ከቀኝ መስመር በኩል ሄኖክ አዱኛ ያሻገረዉን ኳስ አማኑኤል ተርፉ በግንባር ገጭቶ ወደ ግብነት መቀየር ችሏል። ግብ ከተቆጠረባቸው በኋላ የአቻነት ግብ ለማስቆጠር በርከት ያሉ ተጫዋቾችን ቀይረዉ ወደ ሜዳ በማስገባት አንዳች ነገር ለመፍጠር ሲጥሩ የነበሩት ሲዳማዎች በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ላይ ዉጥናቸዉ ሰምሮ የአቻነት ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ሲቀሩ ፤ በተቃራኒው ፈረሰኞቹ በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ላይ ተደጋጋሚ የሚባሉ ሙከራዎች በዳግማዊ አርአያ እና አማኑኤል ተርፉ አማካኝነት ሙከራ ማድረግ ቢችሉም ተጨማሪ ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ጨዋታዉ ቅዱስ ጊዮርጊስ 1ለ0 አሸናፊ ሆኗል።
- ማሰታውቂያ -
በዕለቱ ተጠባቂ መርሐግብር የአሰልጣኝ በፀሎት ልዑል ሰገድ ቡድን ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፋሲል ከነማን 4ለ2 በሆነ ዉጤት አሸንፏል !!
አመሻሽ አስራ ሁለት ሰዓት ላይ በተጀመረዉ እና ማራኪ እንቅስቃሴ በተስተዋለበት የዕለቱ ጨዋታም የዳኛዉ ፊሽካ በተነፋ ገና በ10ኛዉ ደቂቃ አፄዎቹ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል ። በዚህም ከኋላ መስመር የተሻገረለትን ኳስ አጥቂዉ ጌታነህ ከበደ ለአማኑኤል ገ/ሚካኤል አቀብሎት አማኑኤልም ግብ ጠባቂዉን አታሎ በማለፍ ድንቅ ግብ ማስቆጠር ችሏል።
ገና በጨዋታዉ መባቻ ላይ ግብ ካስተናገዱ በኋላ የአቻነት ግብ በማስቆጠር ምላሽ ለመስጠት መታተር የጀመሩት ባንኮች በ27ተኛዉ ደቂቃ ላይ የአቻነት ግብ አጊኝተዋል ፤ በዚህም የፊት መስመር ተጫዋቹ አዲስ ግደይ ኳስ በእጅ በመነካቱ የተሰጠዉን ቅጣት ምት ወደ ግብነት መቀየር ችሏል። የአቻነት ግብ ከተቆጠረባቸዉ በኋላ ወደ ጨዋታዉ ለመመለስ በተደጋጋሚ ጫናዎችን መፍጠር የጀመሩት አፄዎቹ ከአንድ ሁለት ተጠቃሽ ሙከራዎች በኋላ በ38ተኛዉ ደቂቃ ላይ ወሳኝ ግብ ማግኘት ችለዋል ፤ በዚህም ዮናታን ፍስሀ ከቀኝ መስመር በኩል ያሻማውን ኳስ አጥቂዉ ሽመክት ጉግሳ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን በድጋሚ መሪ ማድረግ ችሏል። በማራኪ እና ድንቅ እንቅስቃሴ የቀጠለዉ የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታም የመጀመሪያው አጋማሽ ሊገባደድ ጥቂት ደቂቃዎች ሲቀሩት ዳግም የአቻነት ግብ አስቆጥረዋል ። በዚህም ከቅጣት ምት ኤፍሬም ታምራት ያሻገረዉን ኳስ ካሌብ ወደ ግብነት ቀይሮ አጋማሹ ሁለት አቻ ተገባዷል ።
ከዕረፍት መልስ የተጫዋች ቅያሪ በማድረግ በጨዋታው ላይ ብልጫ ለመዉሰድ መጣር የጀመሩት ባንኮች በ55ተኛዉ ደቂቃ ላይ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል ፤ በዚህም በጨዋታዉ መሐል በተደጋጋሚ ስህተቶችን ሲፈፅም የነበረዉ የአፄዎቹ የግብ ዘብ ይድነቃቸው ኪዳኔ በስህተት ለኪቲካ ያቀበለዉን ኳስ ኪቲካ ለቢኒያም አቀብሎት ተጫዋቹም ወደ ግብነት ቀይሮ መሪ መሆን ችለዋል ።
የጨዋታዉ ደቂቃ እየገፋ በሄደ ቁጥር በማጥቃቱ ረገድ እየተዳከሙ የቀጠሉት አፄዎቹ በ79ነኛዉ ደቂቃ ላይ ድንቅ ሙከራ ማድረግ ችለዋል ፤ በዚህም ተቀይሮ የገባዉ ናትናኤል ገ/ጊዮርጊስ ከጌታነህ ከበደ የተቀበለዉን ኳስ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም የግቡ ቋሚ ኳሷን መልሷታል።
በተቃራኒው የጨዋታዉ ደቂቃ እየገፋ በሄደ ቁጥር ይበልጥኑ ወደ ራሳቸዉ የግብ ክልል አፈግፍገው በመጫወት አልፎ አልፎ የሚገኙ እድሎችን ለመጠቀም ይጥሩ የነበሩት ባንኮች በጭማሪ ደቂቃ ላይ ተቀይሮ በገባዉ ወጣቱ ተጫዋች ዳዊት ዮሐንስ አማካኝነት ተጨማሪ ግብ አክለዉ ጨዋታው በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 4ለ2 አሸናፊነት ተጠናቋል።