ቀን 10:00 ሰዓት ሲል በዋና ዳኛ ማኑኄ ወልደፃዲቅ ፊሽካ በጀመረዉ እና ሁለቱም ቡድኖች ቶሎ ቶሎ ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል በመድረሱ ረገድ ድንቅ ሆነዉ በጀመሩት ጨዋታ ገና በመባቻዉ በ8ተኛዉ ደቂቃ ላይ ሀድያዎች ሙከራ ማድረግ ችለዋል ፤ በዚህም ተመስገን ብርሐኑ ከብሩክ ማርቆስ የተቀበለዉን ኳስ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ፍሬዉ ኳሷን ተቆጣጥሯታል። በድጋሚ ጫና ፈጥረዉ መጫወት የቻሉት ሀድያዎች በ17ተኛዉ ደቂቃ ላይ በአጥቂዉ ዳዋ ሁቴሳ አማካኝነት ከርቀት ድንቅ ሙከራ ማድረግ ቢችሉም ነገር ግን የግብ ዘቡ ዳግም ኳሷን አምክኗል።
በተቃራኒው በሙከራ ረገድ የተቀዛቀዘ የጨዋታ ጊዜ እያሳለፉ የቀጠሉት ኢትዮጵያ ንግድ ባንኮች የመጀመሪያው አጋማሽ ሊገባደድ ጥቂት ደቂቃዎች ሲቀሩት አጥቂዉ ቢኒያም ጌታቸዉ በ41ኛዉ ደቂቃ ላይ ድንቅ ሙከራ ማድረግ ሲችሉ ፤ በድጋሚ በ45ተኛዉ ደቂቃ ላይ ሱለይማን ጥሩ የግብ ዕድል መፍጠር ቢችልም ግብ ሳይቆጠር አጋማሹ ተጠናቋል ።
ከዕረፍት መልስ በጨዋታ እንቅስቃሴ ረገድ ይበልጥኑ ተሻሽለዉ የተመለሱት ኢትዮጵያ ንግድ ባንኮች በ51ኛዉ ደቂቃ ላይ በቢኒያም ጌታቸዉ አማካኝነት ጥሩ ሙከራ ማድረግ ችለዉ ነበር ፤ በዚህም ተጫዋቹ ከግራ መስመር በኩል ከአዲስ ግደይ የተሻገረለትን ኳስ በፎርቢች ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ግብ ጠባቂዉ ፔፔ አልዛየር ኳስን ይዞበታል። ከዚህ ተጠቃሽ የባንኮች ሙከራ ውጭ የጠራ ሙከራ ለማድረግ የተቸገሩት ሁለቱም ክቦች በሁለተኛዉ አጋማሽ ይህ ነዉ የሚባል አደጋ መፍጠር ሳይችሉ መርሐግብሩ 0ለ0 በሆነ አቻ ዉጤት ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
– በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ኤፍሬም ደበሌ መሪነት ምሽት አንድ ሰዓት ሲል በጀመረዉ የምሽቱ መርሐግብር ድሬዳዋ ከተማ ኢትዮጵያ ቡናን 2ለ1 በሆነ ዉጤት ማሸነፍ ችሏል ።
ተመጣጣኝ በሚባል የጨዋታ ፉክክር በጀመረዉ የምሽቱ ጨዋታ ገና በመባቻዉ ድሬዎች ከማዕዘን በተገኘ ኳስ ግብ ለማስቆጠር ተቃርበዉ የነበረ ቢሆንም ከብዙ ንክኪዎች በኋላ ተከላካዩ ወንድሜነህ ደረጀ ኳሷን አውጥቷታል። በዚህ ሂደት ጨዋታቸዉን የጀመሩት ድሬዎች በድጋሚ በ8ተኛዉ ደቂቃ ላይ ድንቅ የግብ ሙከራ ከሳጥን ውጭ አድርገው የነበረ ቢሆንም ኳሷ ግብ ጠባቂዉ በረከት በቀላሉ ተቆጣጥሮታል።
በንፅፅር በሙከራ ረገድ የተቀዛቀዙ ቢሆንም በጨዋታ እንቅስቃሴ ግን ብልጫ የነበራቸው ቡናማዎቹ በ31ኛዉ ደቂቃ ላይ የመጀመሪያ ኢላማዉን የጠበቀ ሙከራ ማድረግ ችለዋል ፤ በዚህም ከቀኝ መስመር በኩል ሱራፌል ጌታቸዉ ያቀበለዉን ኳስ ዘርዓይ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ ለጥቂት ወጥታለች። በድጋሚ በ40ኛዉ ደቂቃ ላይ ከተመሳሳይ ቦታ አብዱልከሪም ወደ ግብ ክልሉ ድንቅ ኳስ አሻምቶ የነበረ ቢሆንም መስፍን ታፈሰ በአስገራሚ ሁኔታ ሳይጠቀምባት ቀርቷል።
ከዕረፍት መልስ ፉክክር ጨምሮ በቀጠለዉ ጨዋታም በ49ነኛዉ ደቂቃ ላይ ድሬዳዋ ከተማዎች መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ አስቆጥረዋል ፤ በዚህም መሐመድ አብዱለጢፍ ያሻገረለትን ኳስ ቻርልስ ሙሰጌ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል ። በዚህ ሂደት በቀጠለው ጨዋታም በ ደቂቃ ላይ ቡናማዎቹ የድሬዳዋ ከተማን ተከላካዮች አለመናበብ ተከትሎ የተፈጠረዉን ስህተት አንተነህ ተፈራ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን አቻ ማድረግ ችሏል።
የጨዋታዉ ደቂቃ እየገፋ በሄደ ቁጥር ተጋግሎ በቀጠለዉ ጨዋታም በ84ተኛዉ ደቂቃ ላይ ድሬዳዋ ከተማዎች ግብ አስቆጥረዉ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ጥፋት መሰራቱን ተከትሎ ጎሉ ቢሻርም መደበኛዉ 90 ደቂቃ ተጠናቆ በተጨማሪ ደቂቃ ድሬዎች የማሸነፊያ ግብ አግኝተዋል ፤ በዚህም በግራ መስመር በኩል መሐመድ አብዱለጢፍ ወደ ግብ የላከዉን ኳስ ግብ ጠባቂዉ በረከት መቆጣጠር አለመቻሉን ተከትሎ ቻርልስ ሙሰጌ ሁለተኛ ግን አስቆጥሮ ክለቡን ድሬዳዋ ከተማ 2ለ1 አሸናፊ ማድረግ ችሏል።