*….ስታዲየሙ ያሉት ንብረቶች የኔ ነው በሚል ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱና ፌዴሬሽኑ እየተወዛገቡ ነው…
*…ቀድሞ የነበሩት የስታዲየሙ ወንበሮች የት እንደደረሱ አልታወቀም….
*….. ኪሎውን ተመዝኖ የመጣው ሲኖትራክ ትሪቩን ውስጥ እንዳለ ተይዟል….
በባህልና ስፖርት ሚኒስቴር በጀት ተይዞለት ዕድሳት ላይ ያለው የአዲሰ አበባ ስታዲየም የውስጥ ብረቶችን በሲኖትራክ መኪና እየጫነ የነበረው ሹፌር ከነ መኪናው በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሏል።
- ማሰታውቂያ -
እድሳቱ የዘገየውና እየተጓተተ የመጣው የአዲስ አበባ ስታዲየም በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዋጋ ያላቸው ንብረቶች በሙሉ ሲጓዙ መቆየታቸው የአደባባይ ሚስጢር እንደነበር የሚናገሩ በርክተዋል። ከትላንት በስቲያ ምሽት አንድ ሲኖትራክ መኪና ስታዲየም ውስጥ በመግባት ከፍተኛ ወጪ ያላቸውን ብረቶች መኪና ውስጥ እየጫነ እያለ የፌዴሬሽን ሰዎች ደርሰውበት ለፖሊስ በተሰጠው ጥቆማ ሹፌሩ የተያዘ ሲሆን መኪናዬ ተመዝኖ የምወስደውን ብረት ጭኜ እንድወጣ ታዝዤ የመጣሁት የሚል ምላሽ ቢሰጥም ከነመኪናው ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወስዶ እዚያው ማደሩ ታውቋል። በዚህ ዝርፊያ ላይ የተጠረጠሩት ግለሰቦችና የባህል ስፖርት ሚኒስቴር ባልደረቦች ትላንት ተይዘው የነበረ ቢሆንም ሚኒስትሩ አቶ ቀጀላ መርዳሳ ያዘዝኩት እኔ ነኝ በማለታቸው ቃላቸውን ከሰጡ በኋላ እንዲለቀቁ መደረጉ ቅሬታ ፈጥሯል።
ሚኒስቴር ደኤታው አምባሳደር መስፍን ቸርነት እሳቸውና ሚኒስትሩ በቦታው ላይ ሳይመጡ ጭምር ብዙ ንብረቶች በመጥፋታቸው ይሄን ብቻ ሳይሆን ከበፊቱ ጀምሮ የነበረው ምዝበራ እንዲጣራ ለሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የህግ ክፍል ደብዳቤ መጻፋቸው ታውቋል። እጅ ከፍንጅ ተያዘ የተባለው ግለስብ ላይ ምርመራው ተጠናክሮ ባለበት ሂደት የስታዲየሙ ጥበቃዎች ቃል ሰጥተው በተመለሱበት ሚኒስትሩ አቶ ቀጀላ “አካባቢውን አጥሩና ለምርቃት አዘጋጁ ብዬ ያዘዝኩት እኔ ነኝ” በማለታቸው የተያዙት ሰራተኞች መለቀቃቸው በሁለቱ አመራሮች መሃል ልዩነት መፈጠሩን ያሳየ ሆኗል።
“አቶ ቀጀላ ያዘዙት ምንድነው..? ቆሻሻዎቹ እንዲጠረጉና አካባቢው ንጹህ እንዲሆን ወይስ ንብረቶቹ እንዲዘረፉ ” የሚሉት ወገኖች ስታዲየሙ ቀድሞ የነበረው ወንበር ብረቶችና የተለያዩ ንብረቶች የት እንዳሉ ሚኒስትሩና ሚኒስቴር መስሪያ ቤታቸው ምላሽ እንዲሰጡበት ይጠይቃሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየምና በአደይ አበባ ስታዲየም የነበሩትን ብረቶችና ንብረቶች የት እንዳሉ የማይታወቅ ሲሆን ምናልባት ለመመዝበሩም ግንባታውን የሚመራው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ፣ አመራሮቹና በቀጥታ የሚመለከታቸው ሃላፊዎች መጠየቅ እንዳለባቸው ተጠይቋል።
የአዲስ አበባ ስታዲየም ውስጥ ያሉት ንብረቶች የኔ እንጂ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አይደለም የሚለው የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን በበኩሉ ከዚህ በፊት የስታዲየሙ ወንበሮች ሲገጠሙ ጨረታውን ያወጣው ፌዴሬሽኑ በመሆኑ ሚኒስቴር መሰሪያ ቤቱ የኔ ነው የሚልበት ምክንያት የለውም በማለት ንብረቶቹ በመመዝበራቸው ማጣራት ተደርጎ ጥፋተኞቹ ላይ ርምጃ እንዲወሰድ ለፖሊስ በደብዳቤ መጠየቁ ታውቋል።
ባለፉት አመታት ከእደሳ ጋር ተያይዞ የኤሌክትሪክ ኬብሎች፣ ብረቶች ወንበሮችና ልዩ ልዩ ንብረቶች ሲወጡ እንደነበር የቅርብ ምንጮች ይናገራሉ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ውሴጥ ያሉ ሰንሰለቶች ካልተበጠሱ የቆየው የንብረት ማሸሽና ዝርፊያ ሊቀጥል ይችላል ተብሎም ተሰግቷል። እስካሁን የተነቀሉት የሙሉ ስታዲየም ወንበሮች ብረቶችና ንብረቶች የት እንደገቡ የማይታወቅ በመሆኑ ሚኒስትሩ አቶ ቀጀላ መርዳሳና የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አመራሮችና ባለሙያዎች ለኢትዮጵያ ህዝብ የት እንዳሉ የማብራራት ግዴታ እንዳለባቸው ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ወገኖች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
የይገባኛሉ ክርክር አሸናፊ ማን እንደሆነ ባይታወቅም የአፍሪካ ዋንጫ ፍጻሜ ላይ እንዲገኙ ካፍ ለአፍሪካ ሀገራት እግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንቶች ባቀረበው ጥሪ መሰረት ወደ አቢጃን ያቀኑት የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ ጅራ ከኮትዲቯር ሲመለሱ ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አመራርች ጋር በሚያደርጉት ውይይት ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል።