በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 7ጨዋታዎች የተደረጉ ሲሆን 6ቱ በክልል አንዱ ደግሞ አዲስ አበባ ላይ ተደርገዋል። ክልል ላይ ከተደረጉት ጨዋታዎች መካከል አንዱ የሆነውን ሲዳማ ቡና ከ መቐለ 70 እ. የነበረውን ጨዋታ በዚህ ሪፖርት ለእናንተ እንዲስማማ አድርገን አቅርበንላችኋል።
እንደ ሌሎቹ ጨዋታዎች ሁሉ 9:00 ሲል የጀመረው እና በፌዴራል አርቢትር አሸብር ሰቦቃ እየተመራ ሲዳማ ላይ የተደረገው የሲዳማ ቡና እና የመቐለ 70 እ. ጨዋታ በእንግዳዎቹ መቐለ 70 እ. 2-1 አሸናፊነት ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
የውድድሩ የአምና ሻምፒዮን መቐለ 70 እ. የመጀመሪያውን ግብ ለማግኘት 20ደቂቃዎች ብቻ የፈጀባቸው ሲሆን የ2011 የውድድር አመት የሊጉ ኮከብ ተጫዋች ተብሎ የተመረጠው አማኑኤል ገ/ሚካኤል ያስቆጠረው ግብ መቐለ 70 እንደርታን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል። የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ 1ደቂቃ ብቻ ሲቀረው 44ኛው ደቂቃ ላይ የመቐለ 70 እንደርታው ያሬድ ከበደ ሌላ ግብ አክሎ 2-0 እንዲመሩ አስችሏል። ሆኖም ግን ከ1ደቂቃ በኋላ 45ኛው ደቂቃ ላይ ሲዳማ ቡናዎች በአበባየሁ ዮሐንስ ግብ ቢያስቆጥሩም ከማስተዛዘኛነት ማለፍ ሳይችል በሜዳቸው በአምናው ሻምፒዮን ሽንፈት ሊያስተናግዱ ግድ ሆኖባቸዋል። የዛሬውን ድል ተከትሎ መቐለ 70 እንደርታ ከመሪው ወልዋሎ አ.ዩ. በ3ነጥቦች አንሶ በ7ነጥቦች 5ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ተሸናፊው ሲዳማ ቡና ደግሞ ከመቐለ 70 እንደርታ በ1ነጥብ ብቻ ዝቅ ብለው በ6 ነጥቦች 6ኛ ደረጃን መያዝ ችሏል።
ሊጉን ወልዋሎ አ.ዩ. በ10 ነጥቦች ሲመራ ፋሲል ከተማ፣ ባህርዳር ከተማ፣ ሀዋሳ ከተማ እና መቐለ 70 እንደርታ በእኩል 7ነጥቦች በግብ ክፍያ ተበላልጠው ከ2ኛ እስከ 5ኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል። የኮከብ ጎል አግቢነቱን ደግሞ የፋሲል ከተማው ሙጂብ ቃሲም በ4 ግቦች ሲመራ አዲስ ግደይ፣ ዳዋ ሁቴሳ እና ሰመረ ሀፍተይ በእኩል 3ግቦች ተከታዩን ደረጃ ይዘዋል።