በሀያ ስድስተኛዉ ሳምንት ሶስተኛ ዕለት ቀዳሚ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንኮች ፋሲል ከነማን በማሸነፍ የሊጉን መሪነታቸዉን አጠናክረዋል።
በዋና ዳኛ ሔኖክ አበበ ፊሽካ ቀን ዘጠኝ ሰዓት ሲል በጀመረዉ ጨዋታ ሁለቱም ክለቦች ቶሎ ቶሎ ወደ ግብ ከመድረስ እና ሙከራዎችን ከማድረግ ይልቅ በአብዛኛዉ ጥንቃቄ በተሞላበት እና በመሐል ሜዳ ላይ በተወሰነ እንቅስቃሴ ጨዋታቸውን ጀምረዋል።
ከተጠበቀዉ በተቃራኒዉ እምብዛም ሙከራዎች ባልተደረጉበት የጨዋታዉ የመጀመሪያ አጋማሽ በ16ተኛዉ ደቂቃ ላይ ሙከራ ተመልክተንበታል ፤ በዚህም ከግራ መስመር በኩል ኤፍሬም ታምራት ያሻገረዉን ኳስ ያገኘዉ ኪቲካ ጀማ ኳሷን በጭንቅላቱ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ኳሷ ኢላማዋን ሳትጠብቅ ወጥታለች።
በ40ኛዉ ደቂቃ ላይ በተመሳሳይ ከግራ መስመር በኩል ኤፍሬም ታምራት ያሻማዉን ኳስ ባሲሩ ዑመር ሲጨርፈዉ ከኋላ ይገኝ የነበረዉ ፉዓድ ፈረጃ ኳሷን አግኝቶ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ኳሷ ለጥቂት በግቡ የቀኝ ቋሚ በኩል ወጥታለች። እምብዛም ሙከራ ባላስመለከተን የመጀመሪያው አጋማሽ ሁለቱም ክለቦች ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ ጨዋታቸዉን ሲከዉኑ ቆይተዉ አንድ ኢላማዉን የጠበቀ ሙከራ ብቻ አስመልክተዉን ለዕረፍት ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።
- ማሰታውቂያ -
ከዕረፍት መልስ ሁለቱም ክለቦች ቅያሪዎችን በማድረግ የጨዋታዉን ቴምፖ ለመቆጣጠር ጥረት ማድረግ ቢቀጥሉም ነገር ግን በተቃራኒው በሙከራ ረገድ እንደ መጀመሪያዉ አጋማሽ ሁሉ ቀዝቃዛ አጋማሽ አሳልፈዋል። በዚህ ሂደት የቀጠለዉ ጨዋታም በመሐል ሜዳ ከሚታየዉ ፍትጊያ በዘለለ ያን ያህል ተጠቃሽ ሙከራ ሳያስመለክተን ቀጥሎ በ82ተኛዉ ደቂቃ ላይ ግን ግብ ተቆጥሮበታል። በዚህም በዚሁ ደቂቃ ላይ ጋቶች ፓኖም ሱለይማን ላይ ጥፋት መስራቱን ተከትሎ በሁለተኛ ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ሲወጣ ይህንኑ የቅጣት ምት ኳስም ፉዓድ ፈረጃ አሻምቶት ተቀይሮ የገባዉ አዲስ ግደይ ወደ ግብነት በመቀየር መርሐግብሩ በባንክ 1ለ0 አሸናፊነት እንዲጠናቀቅ አስችሏል።
በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሲዳማ ቡናን ማሸነፍ ችሏል ።
በኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ አሸብር ሰቦቃ መሪነት አመሻሽ 12:00 ሰዓት ሲል በበርካታ ደጋፊዎች ታጅቦ በጀመረዉ ጨዋታ ሁለቱም ክለቦች የመሐል ሜዳዉን ፍትጊያ ተቆጣጥረዉ አደጋዎቸን ለመፍጠር ገና በጊዜ ጥረት ማድረግ የጀመሩ ሲሆን በ15ተኛዉ ደቂቃ ላይም ሲዳማዎች ቀዳሚ ሙከራ ማድረግ ችለዋል። በዚህም አጥቂዉ ማይክል ከአማኑኤል ተርፉ የቀማዉን ኳስ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ ግብ ጠባቂዉ ባህሩ ነጋሽ ሲመልስ በቅርብ ርቀት ላይ የነበረዉ ይገዙ ቦጋለ ሳይጠቀምባት የቀረችዉ ኳስ በሲዳማዎች በኩል የተደረገች አስቆጭ ሙከራ ነበረች ።
ያን ያህል ሙከራ ባላስመለከተን ጨዋታ በመጀመሪያዎቹ ደቂቃዎች ላይ መጠነኛ ብልጫ የተወሰደባቸዉ ፈረሰኞቹ በግማሽ ሰዓት አንድ ሙከራ ማድረግ ችለዋል። በዚህም ሞሰስ አዶ ለመስመር ተጫዋቹ ተገኑ ተሾመ ያቀበለዉን ኳስ ተጫዋቹ እየገፋ ከግብ ጠባቂዉ መክብብ ጋር ተገናኝቶ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ሳይሳካ ቀርቷል። ያን ያህል በሙከራ ባልታጀበዉ እና ለተመልካችም ሳቢ ባልነበረዉ የጨዋታዉ የመጀመሪያ አጋማሽ አንድም ኢላማዉን የጠበቀ ሙከራ ሳያስመለክተን ክለቦቹ ለዕረፍት ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።
በሁለተኛዉ አጋማሽ ሁለቱም ክለቦች የተጫዋቾች ለዉጥ በማድረግ ብልጫ ለመዉሰድ ጥረት ማድረግ የቀጠሉ ቢሆንም ነገር ግን ያን ያህል አዝናኝ ባልሆነ እንቅስቃሴ ጨዋታዉ ቀጥሎ በ77ተኛዉ ደቂቃ ላይ ከብዙ ጥረት በኋላ ፈረሰኞቹ ግብ አግኝተዋል። በዚህም ተቀይሮ የገባዉ አማኑኤል ኤረቦ ከበረከት ወልዴ የተቀበለዉን ኳስ በግሩም ብቃት ወደ ግብነት መቀየር ችሏል። ከግቧ መቆጠር በኋላ በተመሳሳይ መንገድ በቀጠለዉ ጨዋታዉ መርሐግብሩ ሊጠናቀቅ በጣት የሚቆጠሩ ደቂቃዎች በቀሩበት ወቅት ሲዳማ ቡናዎች በብርሀኑ በቀለ አማካኝነት ከቅጣት ምት ድንቅ ሙከራ ቢያደርጉም ነገር ግን የግብ ዘቡ ባህሩ ነጋሽ ኳሷን እንደምንም አውጥቶ ጨዋታዉ በፈረሰኞቹ 1ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።