እንደ ሰሞኑ መርሐግብር ሁሉ በቅርቡ በድንገት ህይወቱ ላለፈዉ አለለኝ አዘነ የህሊና ፀሎት በማድረግ በጀመረዉ የዕለቱ ጨዋታ ገና በመባቻዉ ሀይቆቹ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ አስቆጥርዋል። በዚህም ከኋላ ክፍል የተቀበለውን ኳስ አሊ ሱለይማን በቀጥታ ወደ ግብ ሲሞክር ግብጠባቂዉ አቡበከር ኑራ በሚገባ መቆጣጠር ባለመቻሉ ምክነያት አጠገቡ የነበረዉ ተባረክ ሄፋሞ ኳሷን መረብ ላይ በማሳረፍ ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል ።
ኢትዮጵያ መድኖች ገና በጊዜ ግብ ከተቆጠረባቸዉ በኋላ ወደ ጨዋታዉ ለመመለስ ኳሱን ተቆጣጥረዉ በመጫወት አደጋዎችን ለመፍጠር ሲጥሩ ፤ በተቃራኒው ጨዋታዉን እየመሩ ያሉት ሀዋሳዎች ደግሞ በተደጋጋሚ አሊ ሱለይማን በሚገኝበት መስመር በኩል ጫና ፈጥረዉ ለመጫወት እና ተጨማሪ ግብ ለማግኘት ሲሞክሩ ተስተውሏል። በዚህ ሂደት በቀጠለዉ ጨዋታም በንፅፅር የበላይነት የወሰዱት መድኖች በ37ተኛዉ ደቂቃ ላይ የአቻነት ግብ አግኝተዋል። በዚህም አጥቂዉ ወገኔ ገዛኸኝ ከጄሬም ፍሊፕ የተቀበለዉን ኳስ ወደ ግብነት ቀይሮ የመጀመሪያው አጋማሽ አንድ ለአንድ በሆነ ዉጤት ተገባዷል።
- ማሰታውቂያ -
ሁለተኛዉ አጋማሽ እንደተጀመረ በ46ተኛዉ ደቂቃ ላይም መድኖች ወደ መሪነት መምጣት ችለዋል ፤ በዚህም በምሽቱ ድንቅ ሲንቀሳቀስ የነበረዉ አቡበከር ሳኒ የሀዋሳ ከተማ ተከላካዮች እና ግብ ጠባቂዉ የፈጠሩትን አለመግባባት ተከትሎ ያገኛትን ኳስ ወደ ግብነት በመቀየር መድንን መሪ አድርጓል። አጋማሹ እንደተጀመረ መመራት የጀመሩት ሀይቆቹም በ58ተኛዉ ደቂቃ ላይ አሊ ሱለይማን ባስቆጠራት ግብ ወደ አቻነት መምጣት ችለዋል።
በ70ኛዉ ደቂቃ ላይ በቶሎ አቻ መሆን የቻሉት መድኖች በያሬድ ካሳየ የቅጣት ምት ኳስ ድንቅ ሙከራ ሲያደርጉ ፤ በአንፃሩ ሀዋሳዎች ደግሞ ከሁለት ደቂቃዎች በኋላ በአሊ ሱለይማን አማካኝነት ድንቅ ሙከራ ቢያደርጉም ኳሷ የግቡን አግዳሚ ነክታ ተመልሳለች።
በመጨረሻም በ86ተኛዉ ደቂቃ ላይ ከርቀት የተገኘዉን ቅጣት ምት አምበሉ በረከት ሳሙኤል በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ ግን ኢላማዋን ሳትጠብቅ ወደ ዉጭ ስትወጣ ፤ በተደጋጋሚ ጥሩ የሚባሉ የግብ ዕድሎችን በመፍጠር ረገድ የተሻሉ የነበሩት መድኖች ዳግም በ89ነኛዉ ደቂቃ ላይ ከኋላ ክፍል በተጣለ ኳስ አቡበከር ሳኔ ግብ ለማስቆጠር ተቃርቦ የነበረ ቢሆንም የግብ ዘቡ ፅዮን መርዕድ ኳሷን በሚገርም ቅልጥፍና ተቆጣጥሯት መርሐግብሩ 2ለ2 በሆነ ዉጤት ፍፃሜዉን አጊኝቷል።