ፋሲል ከነማ በዘንድሮ የውድድር ዓመት ተደጋጋሚ ነጥብ መጣሉና የተለመደውን ውጤታማነት እያጣ መሆኑን ተከትሎ አሰልጣኙ ሃይሉ ነጋሽን ለማሰናበት መወሰኑ ርግጥ ሆኗል።
ከታማኝ ምንጭ በተገኘ መረጃ አሰልጣኙ በዘንድሮ የውድድር አመት 12 ጨዋታ አድርጎ አራት ሲያሸንፍ አራቱን አቻ ወጥቶ በአራቱ ተሸንፎ በ16 ነጥብና 2 ግብ የሰንጠረዡ አጋማሽ 8ኛ ደረጃ ላይ በመገኘት ከመሪው ኢትዮጵያ መድን በ10 ነጥብ መራቁ ቦርዱ የስንብት ውሳኔ እንዲሰጥ እንዳበቃው ከታማኝ ምንጭ የተገኘው መረጃ ያስረዳል። ፕሪሚየር ሊጉ ባለፈው ሃሙስ 13ኛ ሳምንት ጨዋታዎችን በኋላ ለቻን የአፍሪካ ዋንጫ በመቋረጡ በአዳማ የሚደረገው ውድድር እስኪቀጥል ድረስ ፋሲል ከነማ ጥሩ የመዘጋጂያና ከአሰልጣኝ ሃይሉ ጋር ያለውን ሂደት በስምምነት ቋጭቶ ቀጣዩን አሰልጣኝ የመቅጠሪያ ጊዜ ያገኛል ተብሎ ይጠበቃል።
የክለቡ አመራሮችና አሰልጣኙ ተገናኝቸው የተወያዩ ሲሆን አመራሮቹ በስምምነት እንዲለያዩ በቃል ደረጃ ያቀረቡትን ጥያቄ አሰልጣቹ በጽሁፍ አድርጉልኝ ማለቱ ተሰምቷል። የአሰልጣኙ የቅርብ ምንጭ ከክለቡ ጋር ሰኔ 30/2015 ድረስ ያለው ውል ተከብሮ የስድስት ወር ደመወዝ እንዲሰጠው ይፈልጋል ብሏል። አመራሮቹ ሙሉ ድጋፍ አድርገው የሚፈልገውን ተጨዋች አስፈርመውለት ውጤት አለማምጣቱን መናገራቸው አሰልጣኙን እንዳስከፋው ከቅርብ ምንጩ የተገኘ መረጃ ያስረዳል። አሰልጣኙ ትላንት በአመራሮቹ ተጠርቶ ጎንደር በመሄዱ አሁን እየተካሄደ ያለውን የፋሲል ከነማና የሀድያ ሆሳዕና ጨዋታ ጀምሮ ሁለቱ ወገኖች መለያየታቸው ርግጥ ሆኗል።
- ማሰታውቂያ -
የአሰልጣኝ ሃይሉ ነጋሽ /ቲጋና/ ስንብት በፕሪሚየር ሊጉ በአንደኛ ዙር የተሰናበተ አራተኛው አሰልጣኝ አድርጎታል። ከዚህ በፊት የሲዳማ ቡናው አሰልጣኝ ወንድማገኝ ተሾመ፣ የኢትዮ ኤሌክትሪኩ አሰልጣኝ ክፍሌ ቦልተናና የኢትዮጵያ ቡናው አሰልጣኝ ተመስገን ዳና መሰናበታቸው ይታወቃል።