“በኢትዮጵያ እግርኳስ ላይ ትልቅ አስተዋጽዎ ላደረጉ ተጨዋቾች ክብር ቢኖረኝም ማንም ተጨዋች ግን ከሀገር በላይ መሆን አይችልም” ሲሉ የዋሊያዎቹ አሰልጣኝ ውበቱ አባተ ተናገሩ።
አሰልጣኙ ስለቻን ዝግጅት ዙሪያ ለጋዜጠኞች እንደገለጹት “ለ28 ተጨዋቾች ጥሪ አድርገን 26ቱ ተገኝተው ሪፖርት በማድረግ ትላንት ልምምድ ጀምረናል ታፈሰ ሰለሞንና አምበሉ ጌታነህ ከበደ ግን በጊዜው ባለመምጣታቸው ከቡድኑ ውጪ አድርገናቸዋል በሁለቱ ቦታ ሌሎች ይይጠሩ አይጠሩ የሚለውን ከፌዴሬሽኑ ጋር ተነጋግረን የምንወስን ይሆናል በቀጣዮቹ ቀናት ግን በ26ቱ ተጨዋቾች ላይ ትኩረታችንን አድርገን ልምምዳችንን እንቀጥላለን” ሲሉ መልሰዋል።አሰልጣኙ ስለጌታነህ ከበደ በሰጡት ማብራሪያ ” ራሱን ከብሄራዊ ቡድን ስለማግለሉ የሰማሁት እንደማንኛውም ሰው ከሚዲያ ነው በኔ በኩል ግን ጊዜውን ጠብቆ አልመጣም ችግር ገጥሞትም ከሆነ ደውሎ አልተናገረም ሌሎች ቀኑን ሳያከብሩ ሲመጡ እንደተሰናበቱ ተጨዋቾች ጌታነህንም መልሼዋለሁ ታፈሰም ቀኑን አሳልፎ ስለመጣ ተሰናብቷል ይሄ መጋነን የለበትም ማንም ከሀገር በላይ አይደለም” ሲሉ አስረድተዋል።
አሰልጣኝ ውበቱ ” ይሄ አገራዊ ግዳጅ ነው እንደተፈለገ የሚመጣበት አይደለም መከበር አለበት ይሄ ባይፈጠርና ጌታነህ ቡድኑ ውስጥ ቢኖር ደስ ይለኝ ነበር ነገር ግን ሌሎቹ ተጨዋቾች ሰአቱን አሳልፈው ሲመጡ የተወሰነው ውሳኔ ለነጌታነህም የሚሰራ ነው ከዚህ በፊት ተፈጥሮ የነበረው ልዩነት በውይይት ስለተፈታ ከአሁኑ ጉዳይ ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም ብሄራዊ ግዳጅ ላይ እንደመሆናችን ጠንካራ አቋም ሊኖረን ይገባል ተከላካዩ አስቻለሁ ታመነ ከእናቱ ጋር ተያይዞ ከሆቴል ለመውጣት ጥያቄ ያቀረበ ቢሆንም ሳንፈቅድለት በሆቴል እንዲቆይ አድርገናል መሄድ አለብኝ ያለ ሁሉ መሄድ ይችላል ዳግም መመለስ ግን አይቻልም ” ሲሉ መልሰዋል።
የፌዴሬሽኑ ዋና ጸሃፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን በበኩላቸው “ለመንግስት 50 ሚሊዮን ብር ጠይቀን 20 ሚሊዮን 800 ሺህ ተፈቅዶልናል ልዩነቱን ለመሙላት ከስፖንሰሮችና ሌሎች ወገኖች ጋር እየተነጋገርን ነው 26ቱን ተጨዋቾች ጨምሮ 43 የልዑካን አባላት ወደ ውድድሩ ስፍራ ያቀናሉ ብሄራዊ ቡድናችን ጠንካራ ዝግጅት እንደማድረጉና ከሰባት ትልልቅ ቡድኖች አንዱ እንደመሆኑ በቻን ውድድር ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፍ የሚለውን ትተን ያላቸውን አቅም በመጠቀም እስከ ቻሉት ድረስ በመሄድ ታሪክ መስራት የሚል ግብ ተይዟል ፕሬዝዳንታችን አቶ ኢሳያስ ጅራ ከሞሮኮ እግርኳስ ፌዴሬሽን ጋር በተስማሙት መሠረት ከአየር ትራንስፖርት ውጪ በሞሮኮ የዝግጅት ቆይታችን የቡድናችንን ሙሉ ወጪ ሙሉ ለመቻል ተስማምተዋል ስምምነቱ ሁለት የወዳጅነት ጨዋታዎችን እስከ መፈለግ ድረስ ይደርሳል” ሲሉ ተናግረዋል።
- ማሰታውቂያ -
ከቀናት በኋላ ሁለት የወዳጅነት ግጥሚያ ማድረግን ባካተተው ዕቅድ ሙሉ ዝግጅታቸውን ለማድረግ ወደ ሞሮኮ የሚያቀኑት ዋሊያዎቹ ከአዘጋጇ አልጄሪያ ፣ ሊቢያና ሞዛምፒክ ጋር የተደለደሉ ሲሆን የመጀመሪያ ግጥሚያቸውን ጥር 6/2015 ከሞዛምፒክ ጋር እንደሚያደርጉ ይጠበቃል።