“ፌዴሬሽኑ በዋሊያዎቹ ግልጋሎት ላይ የተጎዳን ተጨዋች እንጂ በክለብ ጨዋታ የተጎዳን ተጨዋች የማስመርመር ግዴታ የለበትም”
አሰልጣኝ ዳንኤል ገ/ማሪያም
” የተገኘውን የግብ እድል ባንጠቀምም በአንድ ጎል ሽንፈት የተፈራው መረባችን በበርካታ ግቦች የመሸነፍ ስጋት በመክሸፉ ደስተኛ ነኝ” ሲሉ ውላቸውን ያጠናቀቁት ኢንስትራክተር አሰልጣኝ ዳንኤል ገ/ ማሪያም ተናገሩ።
አሰልጣኝ ዳንኤል ካይሮ ላይ በግብጽ 1ለ0 አሸናፊነት ስለተጠናቀቀው ጨዋታ ዛሬ በሰጡት መግለጫ “በግብጾች የደረሰብን ሽንፈት እኛም ያገኘነውን እድል ባለመጠቀማችን የተገኘ በመሆኑ በቀጣይ ክፍተቱን ለማስተካከል የምንሰራ ይሆናል እነሱ ሰአት ሊፈጁ ሲሞክሩ ስመለከት ማመን አልቻልኩም አዲስ ነገር ሆኖብኛል በቀጣይ የሚመጣው አሰልጣኝ ያለውን የማስቀጠል የጎደለውን በመስራት እንደሚቀጥል ርግጠኛ ነኝ”ሲሉ ተናግረዋል።
- ማሰታውቂያ -
” ሚዲያው እንደሚለው በራስ ግብ ክልል ነው ኳስ የምትቀባበሉት የሚለው የኔን ቡድን አይመለከትም በተጋጣሚ ክልል ላይ ኳስ የሚቀባበል ቡድን የመፍጠር እድል አግኝቻለሁ … የተዘጋ በርን ለማስከፈት ከማንኳኳት ይልቅ በርን የሚየስከፍት መንገድ በመከተል ግብጽን መግጠም ችለናል ከነአን ማርክነህና ጋቶች ፓኖም በግብጽ ክለቦች የመታየት እድል አግኝተዋል” ያሉት አሰልጣኙ “እኔ በማሰለጥነው ቡድን ውስጥ በራስ ግብ ክልል ኳስ በመቀባበል ከምናስቆጥረው ጎል ይልቅ በነሱ ሜዳ ላይ በሚደረግ ቅብብል ግብ ሲቆጠረብን አንገት የምደፋ አይደለሁም ” ሲሉ አስረድተዋል።
ህመም ገጥሞኛል ብሎ ከብሄራዊ ቡድኑ ግልጋሎት ከተገለለ በኋላ በቀናት ውስጥ ለክለቡ ሲጫወት ስለታየው ምኞት ደበበ የተጠየቁት አሰልጣኝ ዳንኤል “ምኞትን በተመለከተ ማላሪያ እንደያዘው የሚገልጸውን የህክምና መረጃውን በቴሌግራም ላከልን ህመሙ 4 ቀን ሙሉ ከየትኛውም ጫና ውጪ እንዲሆን ስለሚያደርገው እኛ ደግሞ ጠንካራ ስራ ስለምንሰራ ተጨዋቹን ከቡድኑ ውጪ አድርገነዋል የሆነው ይሄ ነው ፌዴሬሽኑ በዋሊያዎቹ ግልጋሎት ላይ የተጎዳን ተጨዋች እንጂ በክለብ ጨዋታ የተጎዳን ተጨዋች የማስመርመር ግዴታ የለበትም” ሲሉ አስረድተዋል።
ኢንስትራክተር ዳንኤል ገ/ማሪያምና ምክትላቸው አሰልጣኝ ደግአረገ ይግዛው ከፌዴሬሽኑ ጋር ያላቸው ውል ተጠናቋል። አሰልጣኞቹ በሶስት ወራት ቆይታቸው አራት ጨዋታ ያደረጉ ሲሆን በአሜሪካ ሁለት የወዳጅነት ጨዋታ አድርገው ሲያሸንፉ በሁለቱ የነጥብ ጨዋታዎች ከማላዊ ጋር አቻ ሲለያዩ በግብጽ ተሸንፈዋል።
ዋሊያዎቹ ከወራት በኋላ በአለም ዋንጫ ማጣሪያዎች የሚጠመዱ ሲሆን ቀጣዩ አሰልጣኝ በጥቂትጊዜ ውስጥ የሚታወቅ ይሆናል።